በምርት ዘመኑ የሽምብራ ሰብል በማምረት ተጠቀሚነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን የቀቤና ልዩ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለፁ
በምርት ዘመኑ የፀደይ ወራት የሽምብራ ሰብል በማምረት ተጠቀሚነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የቀቤና ልዩ ወረዳ አርሶ አደሮች ገልጸዋል።
በልዩ ወረዳው 7 ሺ 6 መቶ ሄክታር መሬት በሽምብራ ሰብል መሸፈኑን የልዩ ወረዳው ግብርና ልማት ጽ/ቤት አስታውቋል።
አርሶ አደር ሸምሱ ኡመር፣ መሀመድ ሞሳና ሙባሪክ ሀዲ የቀቤና ልዩ ወረዳ አርሶ አደሮች ናቸው፡፡
የምርት ዘመኑ የበቆሎና የጤፍ ሰብሎችን የመሰብሰብ ስራ በማጠናቀቅ በፀደይ ወራት በመሬቱ ላይ የሽምብራ ሰብል በማምረት ምርታማነታቸውንና ተጠቀሚነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
አሁን ላይ ሰብሉን የመንከባከብ ስራ እየሰሩ መሆናቸውን የሚናገሩት አርሶ አደሮቹ መሬታቸው ለሽምብራ መሬት ምቹና ተስማሚ በመሆኑ ምርታማነታቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ገልፀዋል፡፡
በተለይም በፀደይ ወራት በሽምብራ የተሸፈነ ማሳ ለበልግ እርሻ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥርላቸው መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
አቶ መሀመድአሚን ሸምሱ በልዩ ወረዳው የፈረጀቴ ቀበሌ የግብርና ባለሙያ ሲሆኑ የቀበሌው አርሶአደር የበቆሎና የጤፍ ሰብል የመሰብሰብ ስራ በማጠናቀቅ በማሳው ላይ ሽምብራ እንዲያመርት ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ በመሰራቱ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ገልፀዋል፡፡
ለአርሶ አደሩ በቅርበት ሙያዊ ድጋፍና ክትትል በማድረግ ላይ መሆናቸውንም በመጠቆም፡፡
የቀቤና ልዩ ወረዳ ግብርና ልማት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አብድልሽኩር ደሊል እንደገለፁት በምርት ዘመኑ በፀደይ ወራት 7ሺ 6 መቶ ሄክታር መሬት ሽምብራ ለምቷል።
በተለይም በልዩ ወረዳው በፀደይ ወራት ሽምብራ የሚያመርቱ አርሶ አደሮች ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ እያደገ መምጣቱን ገልፀዋል፡፡
አሁን ላይ የሽምብራ ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ ይገኛል ያሉት አቶ አብድልሽኩር አርሶ አደሩ ሰብሉን የመንከባከብና የመከታተል ስራውን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ገልፀዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ጅላሉ ፈድሉ – ከወልቂጤ ጣቢያችን

More Stories
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርናና ገጠር ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የመስክ ምልከታ እያካሄደ ነው
በዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ ከ154 ሚሊዮን በላይ ዘርፈብዙ ጥቅም ያለቸውን የተለያዩ ችግኞች ለመትከል ዝግጅት መደረጉ ተገለጸ
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በቀቤና ልዩ ወረዳ ምልከታ እያደረገ ነው