ታላቁን የህዳሴ ግድብ ለማጠናቀቅ በቦንድ ግዥ ለመሳተፍና ሙያዊ እገዛ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የጂንካ ቅርንጫፍ ሠራተኞች ገለፁ

ታላቁን የህዳሴ ግድብ ለማጠናቀቅ በቦንድ ግዥ ለመሳተፍና ሙያዊ እገዛ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የጂንካ ቅርንጫፍ ሠራተኞች ገለፁ

የተቋሙ ሠራተኞች በታላቁ የህዳሴ ግድብ ማጠናቀቂያ የቦንድ ግዥ ሀገራዊ ንቅናቄ ላይ ምክክር አድርገዋል።

በዚህም ቀሪ የህዳሴውን ግድብ ለማጠናቀቅ በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የጂንካ ቅርንጫፍ ሠራተኞች ቦንድ ለመግዛት ፈቃደኝነታቸውን አረጋግጠዋል።

ከተቋሙ ጋዜጠኞች መካከል ጋዜጠኛ ወንድማገኝ በቀለ፣ ደፋሩ ስፍታዬና ሌሎች በሰጡት አስተያየት፤ ኢትዮጵያ ታላቁን የህዳሴ ግድብ ስትጀምር ምዕራባውያን ብድርና እርዳታን በመከልከል ለማስቆም ቢሞክሩም ኢትዮጵያዊያን በራሳቸው አቅም እስከ ኃይል ማመንጫ ደረጃ በመድረሳቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልፀዋል።

ቀሪ የግንባታ ስራውን ለማጠናቀቅ በሀገር ደረጃ የተጀመረውን የቦንድ ግዥ ለመቀላቀልና የተለያዩ የዘገባ ስራዎችን በመስራት በሙያቸው ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።

የቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ የልማት ዕቅድ ዝግጅትና ክትትል ቡድን መሪ አቶ ሐብታሙ ጌታቸው ቀሪ የህዳሴውን ግድብ ለማጠናቀቅ ከተቋሙ ሠራተኞች የ120 ሺህ ብር ቦንድ እንደሚገዛ ገልጸው የክፍያ ሁኔታውም እስከ ሰኔ ወር 2017 ዓ.ም ባለው ጊዜ እንደሚጠናቀቅ አስታውቀዋል።

በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የጂንካ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሙሉዋስ ኢትሳ፤ ተቋሙ በአዋጅ ከተሰጠው ሀገራዊና ማህበራዊ ኃላፊነት አንፃር በህዳሴው ግድብም ሆነ በሌሎች ሀገራዊና ማህበራዊ ፕሮጀክቶች ላይ ሠራተኛውን በማስተባበር በሙያውና በመሰል ድጋፎች ተሣትፎውን አጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ሁሴን አለሙ – ከጂንካ ጣቢያችን