በንፁህ መጠጥ ውሀ አቅርቦት እጦት እየተቸገሩ መሆናቸውን በጉራጌ ዞን የገደባኖ ጉታዘር ወለኔ ወረዳ የጅማ ወለኔ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ
የጉራጌ ዞን አስተዳደር በበኩሉ ማህበረሰቡ ላነሳቸው የመሠረተ ልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እየሰራ መሆኑን ገልጿል።
አቶ ኸይሩ አሊ፣ አብድልካፍ አስፋ እና ወ/ሮ ጎሀራም አበራ፤ በገደባኖ ጉታዘር ወለኔ ወረዳ የጅማ ወለኔ ከተማ ነዋሪዎች ሲሆኑ የከተማው ማህበረሰብ በንፁህ መጠጥ ውሀ እጦት እየተቸገረ መሆኑን ተናግረዋል።
ሀያ ሊትር ጀሪካን ለመሙላት እስከ አርባ ደቂቃ ይወስዳል ያሉት ነዋሪዎቹ ለዚህም ከለሊቱ 10:00 ጀምሮ ሰልፍ እንደሚይዙ አንስተዋል።
ለከተማው ማህበረሰብ የንፁህ መጠጥ ውሀ ተደራሽ ለማድረግ የክልሉ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ጥልቅ የጉድጓድ ውሃ ተቆፍሮ ነበር ያሉት የጅማ ወለኔ ስራ አስኪያጅ አቶ ሱልጣን ተማም፤ የጀነሬተሩ የነዳጅ ፍጆታ ከፍተኛ በመሆኑ ማስጠቀም አልቻልንም ብለዋል።
ችግሩን ለመፍታት ማህበረሰቡን በማወያየትና ከወረዳው መንግስት ጋር በጋራ በመሆን ትራንስፎርመር ገዝተናል ያሉት አቶ ሱልጣን፤ በተጨማሪም ለመስመር ዝርጋታና ለፕላን ለሀዋሪያት የደንበኞች አገልግሎት ክፍያ ብንፈፅምም ተቋሙ ችግሩን ሊፈታልን አልቻም ሲሉ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ሆሳዕና ዲስትሪክት የሀዋርያት የደንበኞች አገልግሎት ማዕከል ስራ አስኪያጅ አቶ ጥላሁን ባቢሶ በስልክ በሰጡን ሀሳብ፤ ለውሀ ፕሮጀክቶች ቅድሚያ የሚሰጠው መሆኑን አንስተው አሁን ላይ እየታዩ ያሉ ችግሮች ክልሉ ግብአቶችን በጊዜ ባለማቅረቡ ምክንያት የተፈጠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የጉራጌ ዞን አስተዳደር ልዩ አማካሪ አቶ ዳርጌ ተክሉ በበኩላቸው ማህበረሰቡ የሚያነሳቸው የመሠረተ ልማት ጥያቄዎች መኖራቸውን ገልፀው ችግሩን ለመፍታት ከሆሳዕና ዲስትሪክት እየተነጋገሩ መሆናቸውን አንስተዋል።
አቶ ዳርጌ አክለውም የውሀ ጉዳይ ጊዜ የሚሰጥ ባለመሆኑ በትኩረት እንሰራለን ብለዋል።
ዘጋቢ፡ አስፍር ሙህዲን – ከወልቂጤ ጣቢያችን

More Stories
ከ23 ሚሊየን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ ተገለጸ
በግንቦት እና ሰኔ 2018 ዓ.ም ወራት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ፣ በቱሪዝም፣ በአረንጓዴ ዐሻራ፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ፣ በሀገር በቀል ሪፎርም እና ቀጣናዊ ዲፕሎማሲ ዙሪያ ላይ ያተኮሩ የተለያዩ ከፍተኛ የሥራ ክንውኖችን አድርገዋል።
በህገወጥ መንገድ ከሀገር መውጣት ከህግ፣ ከደህንነት እና ከማህበራዊ አንፃር ከባድ ችግሮችን እንደሚያስከትል ተገለጸ