የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አብርሃም ቲርካሶ እንዳሉት፤ በክልሉ የከተራና የጥምቀት በዓላት በሰላማዊ ሁኔታ ተከብሮ እንዲጠናቀቅ በክልሉ በሚገኙ ሁሉም አካባቢዎች የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ተደርገዋል።
በክልሉ ጥር 10 ማለትም በከተራ በዓል 9 መቶ 24 ታቦታት ከመንበረ ክብራቸዉ ተነስተው ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ስፍራ እንደሚንቀሳቀሱ ምክትል ኮሚሽነር አብርሃም ጠቅሰው፤ ታቦታቱ በሚያልፉባቸው መንገዶች ሁሉ እንቅስቃሴዎችን የሚያስተጓጉሉ ነገሮች እንዳይኖሩ ከሀይማኖት አባቶች፣ ከወጣቶችና ከማህበረሰቡ ጋር ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በክልሉ የከተራና የጥምቀት በዓላት ለተከታታይ 4 ቀናት በተለያዩ ሀይማኖታዊ ክዋኔዎች የሚከበሩ መሆናቸውን ጠቅሰዉ፤ በዓሉን ለማክበር ከሀገር ወስጥም ሆነ ከዉጭ የሚመጡ እንግዶች በሰላም እንዲመለሱ ለማድረግ ህብረተሰቡን ያሳተፈ አስተማማኝ የፀጥታ ስራ እየተሰራ ነዉ ብለዋል፡፡
የከተራና የጥምቀት በዓላት ላይ የስርቆትና ሌሎች ወንጀሎችም ሊከሰቱ ስለሚችሉ ምዕመኑ አስፈላጊዉን ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበትም አሳበዋል፡፡
ህብረተሰቡ በዓሉን ለማክበር በሚያደረገው በማንኛውም እንቅስቃሴ ራሱን ከአደጋ በመጠበቅ ሊሆን እንደሚገባም ተናግረዋል።
ምዕመኑ በዓሉን በሚያከብርበት ወቅት ያልተገባ ድርጊት የሚፈጽሙትን ለፀጥታ አካላት ጥቆማ በመስጠት ትብብሩን እንዲያሳይም ጠይቀዋል።
ምክትል ኮሚሽነር አብርሃም በመጨረሻም ለመላው የእምነቱ ተከታዮች የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ: ተሻለ ከበደ – ከሆሳዕና ጣቢያችን
More Stories
በጤና ዘርፍ የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት ብቁ የሰው ሀይል ወሳኝ ሚና እንዳለው የጤና ሚኒስቴር ገለጸ
በሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ግብርና ጽ/ቤት በክላስተር የቡና ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሀ-ግብር ተካሄደ
በሲዳማ ክልል በዶሮ ዕርባታ ስራ ውጤት ታይቷል አለ የክልሉ እንስሳት ሃብት ልማት ቢሮ