ሕዝቡ ቦንድ በመግዛት ያካበተውን የቁጠባ ባህል በማጠናከር የህዳሴውን ግድብ ግንባታ ሂደት ማሳካት እንደሚቻል ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ጥር 07/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ሕዝቡ ቦንድ በመግዛት ያካበተውን የቁጠባ ባህል በማጠናከር የህዳሴውን ግድብ ግንባታ ሂደት ማሳካት እንደሚቻል የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጂንካ ቅርንጫፍ አስታወቀ።

በኣሪ ዞን በየደረጃው የህዳሴ ግድብ ገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር እየተካሄደ መሆኑም ተጠቁሟል።

ለግድቡ ግንባታ ድጋፍ ለማድረግ በገዙት ቦንድ ገንዘብ በመቆጠብ የተሻለ ገቢ ማግኘት እንደቻሉም ተጠቃሚዎች ተናግረዋል ።

በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የጂንካ ቅርንጫፍ ገሽ ባንክ ስራ አስኪያጅ አቶ ኦርካይዶ ኩሴ እንደገለፁት የህዳሴው ግድብ ኢትዮጵያን ወደ ላቀ ከፍታ ከማድረስ ባለፈ የሕዝብን አንድነትና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን የሚያጠናክር መሆኑን አመላክተዋል።

የህዳሴው ግድብ ግንባታ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በዓይነትም ሆነ በገንዘብ ሰፊ የሕዝብ ተሳትፎ የታየበት ሕዝባዊ ፕሮጀክት መሆኑን ማረጋገጥ የተቻለበት እንደሆነ ኃላፊው አስረድተዋል።

ቀሪውን የግንባታ ሂደት ለማጠናቀቅም ሕዝቡ ያካበተውን የቁጠባ ባህል ቦንድ በመግዛት እንዲያጠናክር አቶ ኦርካይዶ ጥሪ አቅርበዋል።

ቀደም ሲል ለግድቡ ግንባታ ድጋፍ ለማድረግ የቦንድ ግዢ በመፈፀም የቁጠባ አቅማቸውን ማሳደግ የቻሉ አስተያየት ሰጪዎች ቦንድ መግዛት ” በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ …” እንድዲሉ በአንድ ጎን የህዳሴውን ግድብ ግንባታ ሥራ በማገዝ፣ በሌላ በኩል ቁጠባን ማጠናከር መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ለማጠናቀቅ አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ ለማድረግ መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል ።

ዘጋቢ፡ ዳኜ ጥላሁን – ከጂንካ ጣቢያችን