ቤተክርስቲያኗ በተፈጥሮ ሃብት አያያዝና አካባቢ ጥበቃ ረገድ ለዓለም ትልቅ አበርክቶ እንዳላት ተገለጸ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የጌዴኦ አግሮፎረስትሪ ተጠብቆ እንዲቆይ የድርሻዋን እየተወጣች ነው ሲል የጌዴኦ ዞን አስተዳደር ገልጿል።

ዙሪያዋን በሀገር በቀል ዛፎች የተከበበችው የሀንዲዳ መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን ከዲላ ከተማ በ7 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች።

የቤተክርስቲያኗ አስተዳዳሪ መላከሰላም ቀሲስ ጥላሁን ተሰማ ከ40 ዓመት በፊት 4 ሺህ የዛፍ ችግኞችን በማምጣት መትከላቸውን ተናግረዋል።

ቤተክርስቲያኗ ያላት ቅርስም ሆነ ትልቁ ውበቷ ደን ነው ያሉት አቶ መኮንን ሰይፉ፤ ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔ ከማበጀት ባለፈ የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ እየተሰራ እንዳለ ጠቁመዋል።

ትውልድን በስነ-ምግባር ለማነጽ ከዚህ ቀደም ሰሜን ላይ ብቻ የነበረው የአብነት ትምህርት ቤት ለመገንባት ከ60 ሚሊየን ብር በላይ በሀገረ ስብከቱ ተመድቦ እንቅስቃሴ መጀመሩም ተገልጿል።

የሀንዲዳ ደብረሰላም መድሐኒዓለም ቤተክርስቲያን በአካባቢ ጥበቃና የተፈጥሮ ሀብት አያያዝ የበኩሏን እየተወጣች ነው ያሉት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶክተር ዝናቡ ወልዴ፤ በUNESCO ለተመዘገበው አግሮፎረስትሪ በቤተክርስቲያኗ የሚገኙ የረዥም ዘመን ጥብቅ ደኖች ትልቅ አበርክቶ እንዳላቸው ተናግረዋል።

ቤተክርስቲያኗ ከተፈጥሮ ጥበቃ ባለፈ በትምህርቱ ዘርፍ እየሰራች ያለችውን ስራ ዶ/ር ዝናቡ አድንቀዋል።

ዘጋቢ፡ ውብሸት ካሣሁን – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን