የገናና ጥምቀት በዓላትን ምክንያት በማድረግ የህዝብ ፍሰት ከወትሮው የሚጨምር በመሆኑ ህብረተሰቡ ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት እንዲያገኝ የተቀናጀ ስራ እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ ታህሳስ 27/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የገናና ጥምቀት በዓላትን ምክንያት በማድረግ የህዝብ ፍሰት ከወትሮው የሚጨምር በመሆኑ ህብረተሰቡ ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት እንዲያገኝ የተቀናጀ ስራ እየተሰራ መሆኑን የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ጽ/ቤት አስታወቀ።
በዓሉን ከአደጋ ነፃ በሆነ መልኩ ማክበር እንዲቻል ተረጋግተውና የትራፊክ ደንቦችን አክብረው ለማሽከርከር የተቻላቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉ አንዳንድ አሽከርካሪዎች ተናግረዋል።
የሆሣዕና ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ተሾመ ኤርቆጮ እንዳሉት የሆሣዕና ከተማ እንደ ክልልም የህዝብ ፍሰት ከሚበዛባቸው ከተሞች አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፥ በዓላቱን ምክንያት በማድረግ የትራንስፖርት ተገልጋዮች እንዳይጉላሉ ለማድረግ በቂ ውይይት ተደርጎ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል።
የታሪፍና ከወንበር ልክ በላይ የመጫን ችግሮችን ለመቅረፍ በሚያስችል ሁኔታ በመናኸሪያዎቹ በቴክኖሎጂ የታገዘ የትኬት አቆራረጥ ስርዓት መዘርጋቱን የገለጹት ኃላፊው አንዳንድ ከመናኸሪያ ከወጡ በኋላ ጭማሪ በሚያስከፍሉት ላይ እርምጃ እየወሰዱ መሆናቸውን አስድተዋል።
አሽከርካሪዎች የፍጥነት ወሰን ጠብቀው ማሽከርከር እንዳለባቸውና ተሳፋሪዎችም ጥንቃቄ በማድረግ ሊከሰት የምችለውን የትራፊክ አደጋን መከላከል አለባቸው ብለዋል።
በሆሳዕና ከተማ አሮጌውና አዲሱ መናኸሪያ የስምሪት ክፍል አስተባባሪ አቶ ንጉሴ መሼ እና አቶ ታደሰ መሳይ በበኩላቸው በዓሉን ምክንያት በማድረግ ከወትሮ በተለየ ሁኔታ የአጭር ጊዜ እቅድ በማዘጋጀት ለተሳፋሪዎች ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በአሉን ለማክበር ወደተለያዩ አካባቢዎች የሚንቀሳቀሱ ሰዎች የንብረቶቻቸው ደህንነት ተጠብቆላቸዉ መጓዝ እንዲችሉ ከቀይ ለባሾች ጋር በመሆን የተጠናከረ ስራ እየተሰረ እንደሆነም ጠቅሰዋል።
አንዳንድ አሽከርካሪዎች በሰጡት አስተያየት በዓሉን ከአደጋ ነፃ በሆነ መልኩ ማክበር እንዲቻል የትራፊክ ደንቦችን አክብረው ለማሽከርከሩ የተቻላቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።
በመናኸሪዎቹ ውስጥ የትራንስፖርት አገልግሎት ሲያገኙ የነበሩ ተሳፋሪዎችም ያለ እንግልት አገልግሎት ማግኘት መቻላቸውን ገልጸዋል።
አስተያየት ሰጪዎቹ የገና በዓልን ምክንያት በማድረግ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክትም አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ: ተሻለ ከበደ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት ተደራሽ እንዲሆን ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተገለጸ
በክልሉ የተጀመረውን የልማት እና መልካም አስተዳደር ሥራዎችን በማጠናከር የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ከግጭት የጸዳ አካባቢ ለመፍጠር ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሠላም እና ፀጥታ ቢሮ አሳሰበ
በዘመናዊ መንገድ ንብ የማነብ ስራ በመጀመር ውጤታማ መሆናቸውን በወላይታ ዞን የዳሞት ወይዴ ወረዳ ወጣቶች ተናገሩ