የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የክልሉን ሕዝብ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሠራ መሆኑን የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲ ገለጹ

የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 6ኛ መደበኛ ጉባኤውን የካቲት 6 እና 7 2018 ዓ.ም እንደሚያካሂድ ተገልጿል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የክልሉን ሕዝብ በልማት እና መልካም አስተዳደር ሥራዎች ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየሠራ መሆኑን የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲ አብራርተዋል።

የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 6ኛ መደበኛ ጉባኤውን የካቲት 6 – 7/2018 የሚያካሂድ በመሆኑ መላው የክልሉ ምክር ቤት አባላት እንዲገኙ አፈ ጉባኤው ጥሪ አስተላልፈዋል።

በክልሉ በተያዘው በጀት ዓመት በ6 ወራት በክልሉ በተከናወኑ የልማት እና መልካም አስተዳደር ሥራዎች እና ቀሪ ተግባራት ዙሪያ ጉባኤው የሚመክር መሆኑን የገለጹት አፈ ጉባኤው፤ ጉባኤው በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት በቀጥታ ስርጭት የሚተላለፍ በመሆኑ መላው የክልሉ ሕዝብ የሚተላለፉ ውሳኔዎችን በንቃት እንዲከታተል ዋና አፈ ጉባኤው አሳስበዋል።

ዘጋቢ: ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን