የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር የአቶ ጥላሁን ከበደ መልዕክት
እንኳን ለ”ማሮ” የባኔ ብሔረሰብ የአዲስ ዓመት የዘመን መለወጫ በዓል በሰላም አደረሰን! አደረሳችሁ!
በብዝኃነት የተዋበው ኅብረ-ብሔራዊው ክልላችን፤ የየራሳቸው የጊዜ ቀመርና የዘመን መለወጫ በዓላት ያሏቸው ሕዝቦች መገኛ ነው፡፡
ማሮ የባኔ ብሔረሰብ የአዲስ ዓመት የዘመን መለወጫ በዓል፤ በህዝቡ የጊዜ ቀመር መሠረት በወርሃ ታህሳስ አጋማሽ በድምቀት የሚከበር የምስጋና በዓል ነው፡፡
ባህላዊ እሴቱንና ትውፊቱን ጠብቆ የሚከበረው፤ አሮጌውን ዓመት በምስጋና ሸኝተው፤ አዲሱን ዓመት በብሩህ ተስፋ በመቀበል በጋራ ማዕድ የሚቀመስበት፤ የተቸገሩ የሚረዳዱበት የመተሳሰብ እና የአብሮነት በዓል ነው፡፡
ማሮ በባኔ ህዝብ ዘንድ አሮጌውን ዓመት በሰላም እንዲጠናቀቅ ላደረገ ፈጣሪ ምስጋና በማቅረብና መጪው አዲስ ዘመንም የሰላም፤ የፍቅር፤ የአንድነትና የበረከት እንዲሆን በምርቃት አዲሱን ዓመት የሚቀበሉበት ነው፡፡
በዓሉ ከትውልድ ትውልድ ሲሸጋገሩ በመጡ፤ የህዝቡን አብሮነትና አንድነት በሚያጠናክሩ የ ‘ዞምቢያሽካ’ እና የ ‘ደንዛሞ’ ባህላዊ ስርዓቶች፤ የተጣሉ ዕርቅ አውርደው፤ አዲሱን ዓመት በኢባንጋዲ ጨዋታ ታጅበው በደስታና በአብሮነት የሚያከብሩት ድንቅ የክልላችን እሴት ነው፡፡
የሰላም፤ የአንድነትና የመደጋገፍ እሴቶችን ባቀፉ ባህላዊ ክዋኔዎች የታጀበው የማሮ በዓል፤ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ከፍተኛ በመሆኑ ከነሙሉ ባህላዊ እሴቱ ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ማሸጋገር ያስፈልጋል፡፡
በመሆኑም አባቶች ያቆዩልንን ይህን ድንቅ እሴት፤ የአሁኑ ትውልድ ኃላፊነቱን በአግባቡ በመወጣት የበዓሉን ዘመን ተሻጋሪ ባህላዊ እሴቶችና ክዋኔዎች ሰንዶ ለማሻገር መስራት ይጠበቅበታል፡፡
በዓሉ የሰላም፤ የፍቅር፤ የአንድነትና የአብሮነት በዓል እንዲሆንልን እመኛለሁ!!
መልካም በዓል!
ፈጣሪ ሀገራችንንና ሕዝቦቿን ይባርክ
ጥላሁን ከበደ
ርዕሰ መስተዳድር
More Stories
በክልሉ በተያዘው የበልግ ወቅት በኩታገጠም ሩዝና በቆሎ እያለሙ ያሉ አርሶአደሮች ተስፋ ሰጪ የሆነ የምርት ውጤት እንድናይ አስችሎናል አሉ።
ችግር ፈቺ የሆኑ የጥናትና የምርምር ስራዎችን ተግባራዊ በማድረግ የህብረተሰብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አመራር አካዳሚ አስታወቀ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት የሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የተቋማትን የ2017 በጀት ዓመት የማጠቃለያ ዕቅድ አፈፃፀም መገምገም ጀመረ