በደቡብ ኦሞ ዞን በማሌ ወረዳ “ወረዳዊ አንድነት ለዘርፈ ብዙ ዕድገትና ብልጽግና” በሚል መሪ ቃል የምሁራን ምክክር ተካሂዷል፡፡
የማሌ ተወላጅ ምሁራን መካከል በአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሠላምና ፖለቲካል ሳይንስ ትምህርት ክፍል መምህር አቶ ላከዉ ፑልኤ እንዳሉት፤ የአንድን አካባቢ ልማት ለማረጋገጥ ሠላምና ፀጥታን ማስፈን ቀዳሚ ተግባር ነው፡፡
የህዝብ የልማት ጥያቄዎች ባልተመለሱበት ሠላምን ማስፈን አዳጋች መሆኑን በመረዳት ሁሉም የማሌ ተወላጅ ምሁራን፣ ባለሙያዎችና በየደረጃው የሚገኙ አመራር አካላት የበኩላቸውን አስተዋጽኦና ህዝብ የጣለባቸውን ሀላፊነት በታማኝነት መወጣት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል።
የህዝቡን ሠላምና ልማትን ከማረጋገጥ አኳያ መንግሥት ያወጣቸውን ህጎችና አዋጆች የሚጻረሩ አሰራሮችን ለማስቆም የሁሉም ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በማሌ ወረዳ የህግ ባለሙያ አበጄ አዲዮ ናቸዉ።
የደቡብ ኦሞ ዞን ትምህርት መምሪያ ሀላፊ አቶ መልካሙ ሺበሺ በበኩላቸዉ፤ በትምህርት ዘርፉ የሚስተዋለውን የትምህርት ጥራት መጓደል ከማሌ ወረዳም ሆነ ከአጠቃላይ ከደቡብ አሞ ዞን ለመቅረፍ የተሰጣቸውን ሀላፊነት በቁርጠኝነት ለመወጣት ዞናዊ እንቅስቃሴ መጀመራቸውን አስረድተዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ አቶ ዳረጌ ዳሼ፤ የደቡብ ኦሞ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማልኮ እና የማሌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አልጋጋ ባልንሴ የምክክር መድረኩን በጋራ የመሩት ሲሆኑ የማሌን አንድነትና ሠላም በማረጋገጥ የህዝቡን ጥቅም ማስቀደም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በመድረኩ በቀበሌ፣ በወረዳ፣ በዞን፣ በክልልና በፌደራል ተቋማት የሚሰሩ ባለሙያዎችና የአመራር አካላትም የተገኙ ሲሆን የፍትህ እጦት፣ የጤናና የትምህርት የአገልግሎት አሰጣጥ መጓደል፣ በየደረጃው የሚገኙ የአመራር አካላት እና ባለሙያዎች የህዝብን ጥቅም ቅድሚያ ሰጥቶ አለመሥራት፣ ሙስናና ብልሹ አሰራሮች እየተበራከቱ መምጣት፣ የትምህርት ጥራት መጓደል፣ በመድረኩ ተሳታፊዎች የተነሡ ዋና ዋና ነጥቦች ናቸው።
መደረኩ የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቋል፡፡
ዘጋቢ፡ ደኛቸው ደሰ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ