ሀዋሳ፡ ታህሳስ 03/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ምቹና ለኑሮ ተስማሚ አካባቢ ለመፍጠር የተፈጥሮ ሀብትን መንከባከብ ወሳኝ መሆኑን የኮሬ ዞን ግብርና መምሪያ ገለፀ፡፡
በኮሬ ዞን ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ ኮሬና አካባቢ ፕሮግራም ከኮሬ ዞን ደንና አካባቢ ጥበቃ ልማት ጋር በመተባበር ከዞን፣ ወረዳና ከኬሌ ከተማ አስተዳደር ለተውጣጡ ባለድርሻ አካላት በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ስልጠና ተሰጥቷል።
በስልጠናው መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት የኮሬ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አስታረቀኝ አንዳባ እንደተናገሩት፤ በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ ችግሮች ሳቢያ የሚከሰተው የአየር ንብረት ለውጥ ምርታማነትን ለማሳደግ በሚደርገው ጥረት ከፍተኛ ተፅዕኖ ያለው በመሆኑ ተፈጥሮን መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም ኃላፊነት ሊሆን ይገባል።
ጤናማ የሆነ ማህበረሰብ መፍጠር የሚቻለው ከብክለት የፀዳ አካባቢ ሲኖር ነው ያሉት ምክትል አስተዳዳሪው፤ በተፈጥሮ የተሰጠንን ሀብቶች በመጠበቅና በመንከባከብ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ይጠበቅብናል ሲሉ ገልጸዋል።
የኮሬ ዞን ደንና አካባቢ ጥበቃ ልማት ዩኒት አስተባባሪ ወ/ሮ በኃይሏ አሸናፊ በበኩላቸው፤ የአየር ንብረት ተጽዕኖን ለመቋቋምና ለመከላከል የደን ልማትን ማስፋፋትና የደን ሽፋንን መጨመር አማራጭ የሌለው ጉዳይ እንደሆነ አንስተዋል።
በተፈጥሮ ሀብቶች ላይ እየደረሰ ያለውን ጉዳት ለመቀነስ ባለሙያዎች ወደ ማህበረሰቡ በመውረድ የወሰዱትን ስልጠና ተግባራዊ በማድረግ ግንዛቤ እንዲፈጥሩና ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።
ከስልጠናው ተሳታፊዎች መካከል አቶ ሙሴ መንገሻ፣ አቶ ስምኦን ስንታየሁ እና ሌሎችም በሰጡት አስተያየት፤ ከስልጠናው የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ተፈጥሮን የመጠበቅና የመንከባከብ ኃላፊነት የሁላችን እንደሆነ ተረድተን ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በመፍጠር ተቀናጅተን መስራት የሚጠበቅ ተግባር መሆኑን ጠቁመዋል።
ዘጋቢ፡ ለምለም ኦርሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
More Stories
የኢፌዲሪ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ከ82 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ በጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ መቆርቆር ቀበሌ ያስገነባው የንጹህ መጠ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
የኡዱሂያ የዕርድ ስርዓት….የአብሮነት ነፀብራቅ
በቅርቡ በሚሰጠው የ6ኛ እና የ8ኛ ክልላዊ ፈተና ላይ ከ53 ሺህ በላይ ተማሪዎች ለፈተና እንደሚቀርቡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሀዲያ ዞን ትምህርት መመሪያ አስታወቀ