19ኛው የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር በተለያዩ ኩነቶች ተከበረ

19ኛው የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር በተለያዩ ኩነቶች ተከበረ

ሀዋሳ፡ ሕዳር 16/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) 19ኛው የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር በተለያዩ ኩነቶች ተከብሯል፡፡

የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን መከበር ዜጎች በልዩነት መካከል አንድነታቸውን እንዲያጠናክሩ እንደሚያግዝ የበዓሉ ታዳሚዎች ገልፀዋል፡፡

የይርጋጨፌ ከተማ ፐብሊክ ሰርቪስ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ዳዊት የጋ በዓሉን አስመልክቶ ሠነድ ባቀረቡበት ወቅት እንደተናገሩት፤ የፌደራሊዝም አለመዳበር ብዝሃ ማንነቶችን ማስተናገድ ላይ ክፍተቶችን አምጥቷል፡፡

ይሁን እንጂ ዜጎች ልዩነቶችን እንደ እድል ተጠቅመው የነገዋን ኢትዮጵያ በጋራ መገንባት እንደሚችሉም አብራርተዋል፡፡

የይርጋጨፌ ከተማ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ታዬ ታደሰ በበኩላቸው፤ የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን መከበር የሁሉም ብሔር ባህል፣ ቋንቋና ታሪክ እንዲጎለብት ትልቅ አስተዋውፅኦ እንዳለው ተናግረዋል።

እንደ አፈ ጉባኤው ገለጻ፤ የይርጋጨፌ ከተማ ከሃያ ስድስት በላይ ብሔር ብሔረሰቦች የሚኖሩባት መሆኗን በማብራራት ሁሉም የጋራ ማንነቶችን በማዳበር ልዩነቶችን እንደ ፀጋ በመቀበል ለከተማው እድገትና ሠላም የድርሻውን እየተወጣ ነው ብለዋል፡፡

ዘጋቢ፡ አብነት አበበ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን