በክልሉ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ሲከሰቱ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ መሆኑን የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሀ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ።
ቢሮው በሀድያ ዞን ሻሾጎ ወረዳ በጎርፍ አደጋ ለተጎዱ የህብረተሰብ ክፍሎች ድጋፍ አድርጓል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የውሀ፣ መስኖና ማዕድን ኢነርጂ ቢሮ ምክትል ሀላፊና የውሀ ዘርፍ አስተዳደር ዘርፍ ሀላፊ ወይዘሮ አለይካ ሽኩር፤ ባለፈው ጥቅምት ወር በሀድያ ዞን ሻሾጎ ወረዳ በአስራ ሶስት ቀበሌያት በተከሰተው የጎርፍ አደጋ ምክንያት በአካባቢው ያለው የመጠጥ ውሀ በጎርፍ በመበከሉ ለተጎጂዎቹ የንጹህ መጠጥ ውሀ የሚያቀርቡባቸው ቁሳቁስ እና የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁስ ድጋፍ ማድረጋቸውን አስረድተዋል።
ቢሮው የንጹህ መጠጥ ውሀ እንዳይበከል እየሰራ እንደሚገኝና ከተበከለ ደግሞ ውሀውን የማከም ስራ እንደሚያከናውን አስረድተዋል።
በወረዳው በተከሰተው የጎርፍ አደጋም 23 የውሀ ተቋማት በጎርፍ መስመጣቸውን ጠቅሰው ተበክለው የተገኙት የውሀ ተቋማትን የማከም ስራ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
በዚህም ክልሉ 400 ሺህ ብር የሚተመን የአይነት ድጋፍ ማድረጉን አብራርተው ተጎጂዎችም የውሀ ማከሚያ በመጠቀም ራሳቸውን ከተበከለ ውሀ ሊጠብቁ ይገባል ነው ያሉት።
መንግስት አደጋ ከመከሰቱ በፊት ህብረተሰቡን ከተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ አደጋዎች አስቀድሞ የመከላከል ስራዎች ከመስራት ጎን ለጎን ተከስቶ ሲገኝም አስፈላጊውን ድጋፍ ለተጎጂዎች ማድረግ እንደሚገባ አስረድተዋል።
የሀድያ ዞን ውሀ፣ መስኖና ማእድን መምሪያ ሀላፊ አቶ መለሰ ሀይሌ እንደገለጹት በዞኑ በሻሾጎ ወረዳ በጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋ ምክንያት 785 እማወራዎችና አባወራዎች መፈናቀላቸውንና በአካባቢው የውሀ ብክለት እንዳይከሰት የተለያዩ የውሀ ማከሚያዎችን ተደራሽ ተደርጓል።
የክልሉ ውሀ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ድጋፍ በማድረጉ ምስጋናቸውን አቅርበው በአካባቢው ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣትና ተጎጂዎችንም መልሶ ለማቋቋም ሁሉም አካላት የበኩላቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።
በሀድያ ዞን የሻሾጎ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የፋይናንስ ጽህፈት ሀላፊ አቶ በቀለ ዮሴፍ፤ በወረዳው በደረሰው የጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋ ከዞኑና ከክልሉ ጋር በመሆን ከነፍስ ማዳን ስራ ጀምሮ የምግብ፣ የልብስና፣ የድንኳን ድጋፍ ሲደረግ መቆየቱና የክልሉ ውሀ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮው ላደረገው ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ተጎጂዎቹ በሰጡት አስተያየትም የጎርፍ መጥለቅለቅ አደጋው ከተከሰተበት ጊዜ አንስቶ የተለያዩ ድጋፎች እያገኙ መሆናቸውን ገልጸው፤ የክልሉ ውሀ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ላደረገላቸው ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ዘጋቢ፡ መላኩ ንማኒ – ከወልቂጤ ጣቢያችን
More Stories
አካል ጉዳተኞች መብቶቻቸውና ጥቅሞቻቸውን ለማስጠበቅ በቅንጅትና በጥምረት መስራት እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ገለፀ
አካባቢን በመጠበቅና በማጽዳት ምቹና ጽዱ ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት በማገዝ ሁሉም የድርሻውን ልወጣ እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር እንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ አሳሰቡ
ግለሰባዊ ነጠላ ትርክቶችን በጋራ በመታገል በመደመር እሳቤ ችግሮችን መፍታት እንደሚገባ ተገለጸ