የፀረ ተህዋሲያን መድሃኒቶች መላመድ ለሰው ልጆች ስጋት እየሆነ መምጣቱን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታውቋል።
ቢሮው የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ሃላፊዎችና ባለሙያዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የፀረ-ተህዋሲያን መድሃኒቶች በጀርሞች መላመድን መከላከል ላይ ያተኮረ የንቅናቄ መድረክ በቡታጅራ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ የጸረ ተህዋስያን መድኃኒቶች ያለ አግባብ ስራ ላይ በመዋላቸው መድኃኒቶቹ ከተህዋስያን ጋር በቀላሉ እንዲላመዱ እንደሚያስችላቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በመድረኩ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ሀብቴ ገ/ሚካኤል፤ የፀረ-ተህዋሲያን መድሃኒቶች መላመድ ለሰው ልጆች ስጋት እየሆነ መምጣቱን አስታውቀዋል።
በዚህም በየዓመቱ በጸረ ተህዋስያን መድኃኒት መላመድ ምክንያት በዓለማችን ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ለህልፈት እንደሚዳረጉ ሀላፊው አመላክተዋል፡፡
በፀረ ተህዋሲያን መድሃኒቶች መላመድ ምክንያት ብዙ ዋጋ ተከፍሎባቸውና ዓመታትን ወስደው የተገኙ መድሃኒቶችን ዋጋ ቢስ የሚያደርግ ሲሆን ይህም በሽታውን ለማከም አስቸጋሪ እንደሚያደርግ አስረድተዋል፡፡
እንደ ሀገር በዘርፉ እየተስተዋለ ያለውን ችግር ለመቅረፍ ሰፊ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቁመው ለስኬታማነቱ ደግሞ የሁሉም ባለድርሻ አካላት እጅና ጓንት ሆኖ መሥራት ወሳኝ መሆኑን ነው አቶ ሀብቴ ያስገነዘቡት።
ከህዳር 9 እስከ 15 የጸረ ተህዋስያን መድኃኒት በጀርሞች መላመድን ለመቀነስ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሳምንት “እናስተምር፣ እናሳውቅ፣ አሁን እንተግብር” በሚል ሀሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከበረ ይገኛል፡፡
ዘጋቢ፡ መሐመድ ሽሁር – ከወልቂጤ ጣቢያችን

More Stories
እየተከናወነ ያለውን የኮሪደር ልማት ሥራ ከዳር ለማድረስ በሚደረገው ርብርብ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሙዱላ ከተማ አስተዳደር ገለፀ
በትምህርት ሴክተር የመረጃ አያያዝ ውጤታማነት ዙሪያ በኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለጸ
ሁሉንም የመማሪያ መጻሕፍት ባለማግኘታቸው በትምህርታቸው ላይ ጫና እየፈጠረባቸው መሆኑን በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የቆንጋና ቆቄ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተናገሩ