የአካባቢውን ማህበረሰብ መልካም ባህላዊ እሴቶች በማጎልበት ዘላቂ ሠላም ለማስፈን በየደረጃው በተቀናጀ አግባብ መስራት እንደሚያስፈልግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አስታወቀ
በክልሉ ደቡብ ኦሞ ዞን በስፋት አርብቶ አደሮች የሚኖሩበት አካባቢ በመሆኑ ከሕብረተሰቡ አኗኗር ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ የፀጥታ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የማህበረሰቡን ነባርና መልካም ባህላዊ እሴቶችን ማጎልበት ይገባል ያሉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ወላይቴ ቢቶ ናቸው።
ሀላፊዋ አያይዘዉም በአካባቢው በተለያዩ ምክንያቶች ለሚነሱ የፀጥታ ችግሮች መፍትሔ ለመሻት ከተንዛዛ አሰራሮች በመላቀቅ ፈጣን ምላሽ መስጠት ተጨማሪ ችግር እንዳይከሰት ይረዳል ብለዋል።
የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ በበኩላቸው፤ ፀጥታን በማደፍረስ የገቢ ምንጭ የሚያደርጉ ጥቂት አመራሮችን በመለየትና ሠላምን ማስፈን የሁሉንም ብቁ ተሳትፎ ይጠይቃል ብለዋል።
ለፀጥታ ችግሮች መነሻ የሚሆኑ ምክንያቶችንና ወንጀለኞችን ከመቆጣጠር አኳያ ከጎሳ መሪዎችና ወጣቶች ጋር በመሆን በተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት አንፃራዊ ሠላም ማስፈን መቻሉን የዞኑ ሠላምና ፀጥታ መምሪያ ሀላፊ አቶ ጎላ ጉዳቦ እና በዞኑ የሳላማጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኦሌሉ ቻርኒሌይ ገልጸዋል።
አመራሮቹ አክለውም ከማህበረሰቡ ጋር በመቀናጀት በአካባቢው ዘላቂ ሠላም ለማስፈን ቀጣይነት ያለው ሥራ እየተሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል።
ዘጋቢ፡ ዳኜ ጥላሁን – ከጂንካ ጣቢያችን
More Stories
ጥራት ያለው የጤና አገልግሎትን ለማህበረሰቡ ተደራሽ ለማድረግ የጤና ባለሙያዎች በኃላፊነት ሊሰሩ እንደሚገባ በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ
የባስኬቶ ዞን ተወላጆች የአንድነት መድረክ ማጠቃለያ እየተካሄደ ነው
በእንስሳት እርባታ ከተሰማራን ወዲህ ኑሯችን ተሻሽሏል – የጋዘር ከተማ ወጣቶች