በከተሞች የሚስተዋለውን ህገ-ወጥ ግንባታን ከመከላከል እና ህጋዊ አሰራርን ከማስፈን አንፃር ሁሉም አካል የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርኘራይዝ ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ አሳሰቡ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሰረ ልማት ቢሮ የመሬትና ቤቶች ልማት አስተዳደር ኤጀንሲ፤ በከተሞች የሚስተዋለውን ህገ-ወጥ ግንባታና መሬት ወረራ ለመከላከልና ህጋዊ ስርዓት ለማስያዝ የሚያስችል ምክክር ተደርጓል።
የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብርሀኑ ዘውዴ፤ መሬት ለሁሉም ግብዓት መሰረት መሆኑን አውስተው ለልማት እንቅፋት ይሆናልና ህግንና ስርዓትን በማስፈን ህገ-ወጥነትን በህጋዊ አሰራር አደብ ማስያዝ ይገባል ብለዋል።
በየደረጃው የምንገኝ አመራሮችም ወደ ተጨባጭ እርምጃ በመሸጋገር ሁሉን አቀፍ ለውጥና ዕድገት በከተሞች ማስመዝገብ ይጠበቅብናል ሲሉ አሳስበዋል።
በዕለቱ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርኘራይዝ ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ፤ ከተማን መምራትና ማስተዳደር ውስብስብ መሆኑን ጠቁመው መሬትን ለህዝብ፣ ለመንግስትና ለመሰረተ ልማት አገልግሎት ማዋል ያሻል ሲሉ ገልፀዋል።
ከተማ ከጅምሩ ፕላኑ ተጠብቆ ካልተገነባ የሀገርንና ህዝብን ኢኮኖሚ ይጎዳል ብለው በከተሞች ከፕላን ውጪ የሆኑ ግንባታዎችን ወደህጋዊ አሰራሩ ማስገባት እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።
ከኮሪደር ልማት ጋርም የሚስተዋሉ ክፍቶችን በህጋዊ አሰራር በማረምና ችግሮችን ከስሩ መፍታት እንደሚያሻ የተናገሩት አቶ ገብረመስቀል ጫላ በገጠርም ውጤታማ የሆነ የግብርና ስራ እንዲሰራ ተጨባጭ ተግባራት መከናወን አለባቸው ብለዋል።
በቀጣይ በከተሞች መሬት ዘርፍ የሚስተዋለው ህገ-ወጥ የመሬት ወረራና ግንባታን ለመከላከል እና ህጋዊ ስርዓት ለማስያዝ የሚያስችል ሰነድ በዶክተር ጳውሎስ በርጉዴ ቀርቦ ዉይይት ይደረጋል።
በምክክር መድረኩ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርኘራይዝ ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብርሀኑ ዘውዴ፣ ከፍተኛ አመራሮች፣ የመምሪያ ኃላፊዎች ከንቲባዎችና ጥሪ የተደረገላቸው አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ።
ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ
በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ የማህጸን በር ጫፍ ካንሰር ምርመራ እና ልየታ ተካሄደ