ሰሞኑን በጫሞ ሐይቅ ላይ በደረሰው የጀልባ መስጠም አደጋ ከሞቱት ሰዎች የ12 ሰዎች አስከሬን መገኘቱን የጋሞ ዞን ፖሊስ መምሪያ ገለጸ
ከኮሬ ዞን አቡሎ አልፋጮ ወደ አርባምንጭ ከተማ 16 ሰዎችን እና ሙዝ ጭና ስትጓዝ የነበረች ጀልባ ባሳለፍነው ሐሙስ 10 ሠዓት ከ20 ደቂቃ ገደማ ጫሞ ሐይቅ ላይ መስጠሟን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
በአደጋው ምክንያት አስከሬናቸውን በመፈለግ የቆየው የዞኑ ፖሊስ እስካሁን የ12 ሰዎችን አስከሬን ማግኘቱን አስታውቋል፡፡
የዞኑ ፖሊስ መምሪያ የሕዝብ ግንኙነት እና ገጽታ ግንባታ ዲቪዥን ሀላፊ ኮማንደር ረታ ተክሉ እንዳስታወቁት፤ በአደጋው ከተጎዱት ሰዎች 3ቱ በሕይወት ሲገኙ የ12 ሰዎች አስከሬን ተገኝቶ ለቤተሰቦቻቸው ተልኳል።
የዞኑ ፖሊስ ከአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ፖሊስ አባላት ጋር እና ከሌሎች የጀልባ ባለቤቶች ጋር በቅንጅት ቀሪ የአንድ ሰው አስከሬን ፍለጋ መቀጠሉን ሀላፊው ገልጸዋል።
ከአቅም በላይ መጫን ለአደጋው መንስኤ መሆኑንም ኮማንደር ረታ ጨምረው ገልጸዋል።
ዘጋቢ፡ ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን

More Stories
የሴቶች ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ በስፖርትና ባህል ልማት ዘርፍ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ለማሳደግ አበክሮ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
ህግና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የክልሉን ፍትህ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት ሥራ አፈፃፀም አደመጠ
ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እንደሚሠራ የዲላ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ