የቡናና ቅመማ ቅመም ጥራት ደረጃን በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ እየተሠራ ነው

የቡናና ቅመማ ቅመም ጥራት ደረጃን በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ እየተሠራ ነው

ሀዋሳ፡ ጥቅምት 06/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቡናና ቅመማ ቅመም ጥራት ደረጃን በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ እየሠራ መሆኑን የኣሪ ዞን ግብርና መምሪያ ቡናና ቅመማቅመም ፅህፈት ቤት ገለፀ፡፡

ፅህፈት ቤቱ የአምራቹን የቡና ምርታማነት ጥራት ለማሳደግ የሚያግዝ የባለድርሻ አካላት ምክክር መድረክ በጂንካ ከተማ እያካሄደ ነው፡፡

የአሪ ዞን ቡናና ቅመማቅመም ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ርብቃ እሳቱ እንደገለጹት “የሙሉ ፓኬጅ ትግበራ ለቡና ምርትና ምርታማነት፣ ዕድገት ለምርት ማሻሻያ” በሚል መሪ ቃል በዘርፉ በ2017 በጀት አመት የምርት ጥራት ላይ ትኩረት በማድረግ እስከታችኛው መዋቅር ግብረኃይል በማቋቋም እየተሠራ እንዳለም አስረድተዋል ፡፡

በዞኑ ከ20 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በቡና መሸፈኑን አንስተው ያረጁ ቡናዎችን በመጎንደልና አዳዲስ የቡና ዝሪያዎችን በማምጣት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና ምርታማነትን ለመጨመር እየተሠራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

የአሪ ዞን ምክትል አስተዳደርና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ታፈሰ ተሰፋዬ እንዳስረዱት በቡና ግብይት ሥርዓት የሚስተዋሉ ሕገ ወጥ አሠራሮችን በመቅረፍ ዞኑ የራሱ ጣዕም ያለው ቡና በማቅረብ በመላው ዓለም እንዲታወቅ በጥራት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ ይሠራል ብለዋል፡፡

የቡና ጥራትን ለማሳደግ የአመለካከት ችግሮችን በጋራ በመፍታት በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ ለመሆን ሙሉ ፓኬጅን በቡና ምርት ላይ መተግበር እንደሚያስፈልግ የገለፁት የአሪ ዞን ብልፅግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ ናቸው፡፡

ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን