የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት አዲስ የፍርድ ቤቶች መዋቅር ዘርግቶ ወደ ተግባር ለመግባት መዘጋጀቱን አስታወቀ

የደቡብ ምዕራብ ክልል አዲስ የተደራጀ እንደመሆኑ መጠን የክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት  ቀደም ሲል ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ህዝቦች ክልል መንግስት  ሙሉ መዋቅሩን በመውሰድ የህግ ተርጓሚ የዳኝነት መዋቅር እንዳለ በመቀበል ሲጠቀምበት መቆየቱን የደቡብ ምዕራብ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዘዳንት አቶ ቆጭቶ ገብረማርያም የተናገሩት።

መዋቅሩ የአዲሱን ክልል ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ ባለመሆኑ ክልሉ የዳኝነት አካል መዋቅሩን ከክልሉ ህገ መንግስት፣  ከፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ ፣እንዲሁም ከክልላዊ ነባራዊ ሁኔታዎች ጋር በማጣጣም ቀልጣፋ ውጤታማ ተገልጋይ ተኮር ወጪ ቆጣቢ እና ቴክኖሎጂ የተላበሰ የዳኝነት አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ለማድረግ በአዲስ መዋቅር ተቋሙን መገንባት አስፈልጓል ብለዋል።

መዋቅሩን ለማስጠናት የጥናት ብድን ተቋቁሞ ወደ ተግባር ገብቶ ሲሰራ  መቆየቱን የተናገሩት የፍርድ ቤቱ ፕሬዘዳንት አቶ ቆጭቶ ገብረማርያም ጥናቱ ከባለድርሻ አካላት ውይይት ተደርጎ ግብአት ተሰብስቦ ዳብሮ ወደ ስራ እንደሚገባም ነው የተናገሩት።

የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ምክትል ፕሬዘዳንት እና የጥናት ቡድኑ ሰብሳቢ አቶ ጥላሁን ታደመ በበኩላቸው ፍርድ ቤቱ ስራውን ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የታዩ ጥንካሬ እና ጉድለቶችን ለመለየት ኮሚቴ ተዋቅሮ ግብአቶችን ማሰባሰብ መቻሉንም ገልጸዋል።

በተለይም አፋጣኝ እና ቀልጣፍ የዳኝነት አሰራር ለማከናወን ያሉትን የመዋቅር ችግሮች የዳኝነት ነጻነት የቢሮ አደረጃጀት እና የባለሙያ ውስንነት የሚሉት ተግዳሮቶች መለየት ተችሏልም ብለዋል።

ጥናቱም ከተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የተወጣጡ ሙሁራኖች የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች የጠበቃ ሰብሳቢዎች በተገኙበት እንዲሁም ከተለያዩ አለም ሀገራት ልምድ እና ተሞክሮ በማየት መረጃ መሰብሰቡን አስታውቀዋል፡፡

ተሳታፊዎችም በመዋቅሩ ላይ ቢጨመር ወይም ቢስተካከል ያሉትን ሀሳቦች አንስተዋል።

ዘጋቢ: አብዮት በቀለ- ከሚዛን ቅርንጫፍ