በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ በወጣቶች የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት ከ9 ነጥብ 9 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ ማዳን መቻሉ ተገለጸ

በከተማው የወጣቶች የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት ማጠቃለያና የበጋ በጎ ፈቃድ ስራ ማስጀመሪያ መድረክ ተካሂዷል፡፡

 በምክትል ከንቲባ ማዕረግ  የሳውላ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ስራ አስኪያጅ አቶ ፍጹም ጳውሎስ ወጣቶች በትምህርት ጊዜያቸው የቀሰሙትን ዕውቀትና ልምድ በመጠቀም ወሳኝ በሆኑ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መስኮች በመሰማራት ለህብረተሰባቸው ያላቸውን ተቆርቋሪነት አሳይተዋል ብለዋል

ይህንን ተግባር በባለቤትነት የመሩና ያስተባበሩ ባለድርሻ አካላትንና  ወጣቶችን አመስግነዋል።

የሳውላ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አንተነህ አዳነ በበኩላቸው ወጣቶች በክረምት ወራት በተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች በመሰማራት ወገንና ሀገርን ከመርዳት ባሻገር የዕረፍት ጊዜያቸውን አልባሌ ቦታ ከማሳለፍ መቆጠባቸውን ገልጸዋል።

በክረምቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ13 ሺ 600 በላይ ወጣቶችን በማስተባበር በ17 ዘርፎች ተሰማርተው ከመንግሥትና ከህብረተሰቡ ይወጣ የነበረ  ከ 9 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ማዳን መቻሉን ተናግረዋል፡፡

ወጣቶቹ ለአገርና ለወገን ያላቸውን ፍቅርና የኃላፊነት ስሜት  ያሳዩበት ተግባር መሆኑንም አንስተዋል።

የጽ/ቤቱ ምክትል ሀላፊና የወጣቶች ዘርፍ ኃላፊ አቶ ምንያህል ባቤና በበኩላቸው በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት 44 ሺህ 500  የሕብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

በክረምቱ ተጀምረው ያልተጠናቀቁ ስራዎችን ጨምሮ ሌሎች በርካታ ተግባራት በበጋው የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ለማከናወን ስለመታቀዳቸው አብራርተዋል።

በመርሃ ግብሩ ለአቅሜ ደካማ እናት በሰዝጋ ቀጠና በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት የተሰራ መኖሪያ ቤት ርክብክብ ተደርጓል።

ያነጋገርናቸው የከተማው ወጣቶች በሰሩት በጎ ተግባር የህሊና እርካታ ማግኘታቸውን ጠቅሰው ወደፊትም መልካም ተግባርን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።

በመድረኩ ለተግባሩ መሳካት የላቀ አስተዋጾ ላበረከቱ ባለድርሻ አካላት ዕውቅ ተሰጥቷል።

ዘጋቢ፡ አይናለም ሰለሞን – ከሳውላ ጣቢያችን