የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የ2017 ዓ.ም የችሎት ስራ ማስጀመሪያ መድረክ በሚዛን አማን ከተማ ተካሂዷል።
የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የችሎት ስራ ማስጀመሪያ መድረክ ላይ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ፕሬዝዳንቶች፣ የክልሉ ፍትህ ቢሮ ምክትል ሀላፊዎች፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞችና ሰራተኞች እንዲሁም የክልሉ ጠበቆች ማህበር ፕሬዝዳንቶችና ሥራ አስፈጻሚዎች በተገኙበት ተካሂዷል።
በዚህ መድረክ ላይ ከዚህ ቀደም በስራ ላይ ላጋጠሙ ችግሮች መፍትሔ ሊሆኑ የሚችሉ ጉዳዮችን የሚዳስስ ስልጠና ሰነድ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።
የጠቅላይ ፍርድ ቤት የ2017 የችሎት ሥራ በይፋ መጀመሩን ያበሰሩት የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ፕሬዝዳንት አቶ ቆጭቶ ገብረማሪያም፤ ያሉትን ክፍተቶች በመሙላት ቀጣይ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት ታስቦ መድረኩ መዘጋጀቱን ገልጸዋል።
በችሎት አካባቢ ከጅምር እስከ መጨረሻ መከወን ያለባቸውን ጉዳዮች ያካተተ የችሎት አመራር መመሪያ መዘጋጀቱንም አብራርተዋል።
ማህበረሰቡም ወደ ፍርድ ቤት ሲመጣ ያለፍርሃትና ያለስጋት ፍርድ ቤት መጥቶ አገልግሎት አግኝቶ መመለስ እንዲችል መስራት እንደሚገባም ፕሬዝዳንቱ አስገንዝበዋል።
ለዚህም የተዘጋጀውን የችሎት አመራር መመሪያን መተግበርና ማስተግበር ከመላው የጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰራተኞች የሚጠበቅ ተግባር መሆን አለበት ብለዋል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው የቀረበው የግንዛቤ ማስጨበጫ ለቀጣይ ስራ አጋዥ መሆኑን ጠቁመው በተለይ የታችኛው መዋቅር ፍርድ ቤቶችም የሚስተዋልባቸውን ክፍተት አስተካክለው ተገቢውን አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ ተመሳሳይ ስልጠና መውሰድ እንደሚገባቸው ጠቁመዋል፡፡
የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ጥላሁን ታደመ፤ ችሎትን ለችሎት ስራ ምቹ ከማድረግ ረገድ ረጅስትራል ሀላፊነት በመውሰድ ህጉን ተግባራዊ እንዲያደርጉ አስገንዝበዋል።
ዘጋቢ፡ ወሰኑ ወዳጆ – ከሚዛን ጣቢያችን

More Stories
ህብር ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ የምርጫ ማኒፌስቶ፣ የዕጩ ማስተዋወቂያ እንዲሁም የምርጫ ቅስቀሳ ፕሮግራም በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ አካሄደ
ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ጥራት ያለው የአይን ህክምና በሀገሪቱ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየሰራ መሆኑ ተገለፀ
ብልጽግና ፓርቲ የማህበረሰቡ ችግር የሚቀርፉ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ በማጠናቀቅ በውጤታማነት ለአገልግሎት እያበቃ ነው – ዶ/ር መሀመድ ኑርዬ