ሀዋሳ፡ መስከረም 21/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) 12ኛው የኢትዮጵያ ህብረ-ህዋስ ባንኮች ዓመታዊ ጉባኤ “ዘላቂ ፋይናንስ ለጠንካራ የደም እና ህብረ-ህዋስ አገልግሎት” በሚል መሪ ቃል በአርባምንጭ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
ባለፉት በርካታ ዓመታት የህብረ-ህዋስ አገልግሎት የቆመለትን እና ህይወት የመታደግ አላማን ለማሳካት በርካታ ተግባራትን እያከናወነ መቆየቱ ተመላክቷል።
በመድረኩ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ም/ኃላፊ አቶ ናፍቆት ብርሀኑ እንዳሉት፤ በክልሉ የደምና የህብረ-ህዋስ አገልግሎትን ለማሻሻልና የደም ለጋሾችን ቁጥር ለማሳደግ ተጨባጭ ተግባራት ተከናውነዋል።
በቀጣይም የአገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን የፋይናንስ ችግርን መፍታት እንደሚያሻ ኃላፊው ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ህብረ-ህዋስ ደም ባንክ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አሸናፊ ታዘበው በበኩላቸው አገልግሎቱ በ2016 በጀት ዓመት ከዕቅድና ከፍላጎት አንፃር የተሻለ አፈፃፀም ማስመዝገብ መቻሉን ተናግረዋል።
በተያዘው በጀት ዓመትም አገልግሎቱን ከማዘመንና ጥራትን ከማሳደግ አንፃር የሚስተዋለውን የፋይናንስ ችግር ለመፍታት ትኩረት እንደሚደረግ ጠቁመው ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳደግ እንደሚሰራ ገልጸዋል ዶ/ር አሸናፊ።
የአገልግሎቱን የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀምን በተመለከተ ረፖርት ለመድረኩ ቀርቧል።
በመድረኩ በ2016 የላቀ አፈፃፀም ያስመዘገቡ የደም ባንክ አገልግሎቶች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ተጀመረ
የተቀናጀ የመሬት አጠቃቀም ዕቅድ ያረጁ ቡናዎችን ለማደስና አዲስ ተከላን ለማስፋፋት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ
የስራና ክህሎት ቢሮ የቴክኒክና ሙያ ተቋማትን አቅም የሚያሳድግ የ12.8 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አደረገ