ሀዋሳ፡ መስከረም 21/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) 12ኛው የኢትዮጵያ ህብረ-ህዋስ ባንኮች ዓመታዊ ጉባኤ “ዘላቂ ፋይናንስ ለጠንካራ የደም እና ህብረ-ህዋስ አገልግሎት” በሚል መሪ ቃል በአርባምንጭ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
ባለፉት በርካታ ዓመታት የህብረ-ህዋስ አገልግሎት የቆመለትን እና ህይወት የመታደግ አላማን ለማሳካት በርካታ ተግባራትን እያከናወነ መቆየቱ ተመላክቷል።
በመድረኩ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ም/ኃላፊ አቶ ናፍቆት ብርሀኑ እንዳሉት፤ በክልሉ የደምና የህብረ-ህዋስ አገልግሎትን ለማሻሻልና የደም ለጋሾችን ቁጥር ለማሳደግ ተጨባጭ ተግባራት ተከናውነዋል።
በቀጣይም የአገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን የፋይናንስ ችግርን መፍታት እንደሚያሻ ኃላፊው ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ህብረ-ህዋስ ደም ባንክ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አሸናፊ ታዘበው በበኩላቸው አገልግሎቱ በ2016 በጀት ዓመት ከዕቅድና ከፍላጎት አንፃር የተሻለ አፈፃፀም ማስመዝገብ መቻሉን ተናግረዋል።
በተያዘው በጀት ዓመትም አገልግሎቱን ከማዘመንና ጥራትን ከማሳደግ አንፃር የሚስተዋለውን የፋይናንስ ችግር ለመፍታት ትኩረት እንደሚደረግ ጠቁመው ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳደግ እንደሚሰራ ገልጸዋል ዶ/ር አሸናፊ።
የአገልግሎቱን የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀምን በተመለከተ ረፖርት ለመድረኩ ቀርቧል።
በመድረኩ በ2016 የላቀ አፈፃፀም ያስመዘገቡ የደም ባንክ አገልግሎቶች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን

More Stories
የአፍላ ወጣቶችና ወጣቶችን የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ለመቅረፍ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጎልበት የጤና አደረጃጀቶችን ሚና ማሳደግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ
ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የመግባት ዕድል ያገኙ ተማሪዎች የበለጠ ውጤታማ ለመሆን ትምህርታቸው ላይ ብቻ ሊያተኩሩ እንደሚገባ መልዕክት ተላለፈ
የሀዲያ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ለ2018 በጀት ዓመት ከ10 ቢልዮን ብር በላይ በጀት ለተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲውል በተገቢው እንደሚሠራ ገለፀ