ሀዋሳ፡ መስከረም 10/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በወላይታ ዞን የጊፋታ ሩጫ “የጊፋታ እሴቶች ለሁለንተናዊ ብልፅግና” በሚል መሪ ቃል የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር በሶዶ ከተማ ተካሂዷል።
የክልሉ ሠላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ወገኔ ብዙነህ ባስተላለፉት መልዕክት ጊፋታ አዲስ ተስፋን የምንሰንቅበት፣ ትናንት የነበረውን ቂምና ቁርሾን ይቅር መባባሉን የሚያበስር ነው።
ጊፋታ በዓል መለያየትን ሳይሆን መቀራረብን፣ ጥላቻን ሳይሆን ፍቅርንና ሠላም የምንዘከርበት ታላቅ ክብረበዓል እንደሆነም ተናግረዋል።
ይህንን የጊፋታ እሴቶችን በአግባቡ በመጠቀም ለዘላቂ ሀገር ግንባታና ሠላም እንዲሁም የህዝቦችን አብሮነትን፣ ወንድማማችነት እና ለገዢ ትርክት መጠቀም ያስፈልጋል ብለዋል።
ታላቁን የዘመን መለወጫ ጊፋታ በዓላችንን በመንተራስ የምናካሂደው ይህ ሩጫ ቀጣይ የሚያደርገው ደማቅና ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያለው ማህበራዊ ክዋኔ ተደርጎ የሚወሰድ መሆኑን አመላክተዋል።
ሁነቱ እንደ ታላቁ የህዝባችን የዘመን መለወጫ ጊፋታ በዓላችን ሁሉ ለሰላማዊ ዕሴት ግንባታ እና ለወዳጅነት መጎልበት ብሎም ለጠንካራ ሀገረ መንግስት ግንባታ ጉልህ ሚና እንደሚጫወት ታምኖበት የተዘጋጀ ፕሮግራም እንደሆነም ገልጸዋል።
ታላቁ የጊፋታ ሩጫን ጨምሮ የተለያዩ አካላዊ እንቅስቃሴዎች በመኖሪያና በስራ ቦታዎቻችን ዘወትር አቅደን በማከናወን ጤናማና አምራች ዜጋ በመሆን ለሀገር ልማት ጉልህ ሚና ይጫወታል ነው ያሉት።
የጊፋታ ዕሴቶች ለሁለንናዊ ብልፅግናችን የሚለው መፈክር ገብራዊ ሊሆን የሚችለው ሰላማዊና ጤናማ አስተሳሰብ በመገንባት እንደሆነም አስገንዝበዋል።
ሰላማችንና አንድነታችንን ከተንከባከብንና ከተባበርን እኛን ኢትዮጵያዊያንን ማንም አይረታንም ብለዋል።
መርሀግብሩ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ያበረከቱ አካላትን ምስጋና አቅርበዋል።
የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ዶ/ር ፍሬው ሞገስ በበኩላቸው ታላቁ የጊፋታ ሩጫ በውቢቷ ወላይታ ሶዶ ከተማ በመካሄዱ ጠቀሜታው ዘርፈብዙ እንደሆነም ገልፀዋል።
ዘጋቢ፡ ሰላሙ ማሴቦ – ከዋካ ቅርንጫፍ

More Stories
ህብር ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ የምርጫ ማኒፌስቶ፣ የዕጩ ማስተዋወቂያ እንዲሁም የምርጫ ቅስቀሳ ፕሮግራም በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ አካሄደ
ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ጥራት ያለው የአይን ህክምና በሀገሪቱ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየሰራ መሆኑ ተገለፀ
ብልጽግና ፓርቲ የማህበረሰቡ ችግር የሚቀርፉ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ በማጠናቀቅ በውጤታማነት ለአገልግሎት እያበቃ ነው – ዶ/ር መሀመድ ኑርዬ