የዘይሴ ብሔረሰብ  የዘመን መለወጫ ” ቡዶ ከሶ” በዓል  በድምቀት  ተከበረ

ሀዋሳ፡ መስከረም 09/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የአንድነት፣ የመቻቻል እና የእርቀ ሰላም ማብሰሪያ የሆነው የዘይሴ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ ” ቡዶ ከሶ” በዓል  በድምቀት  ተከበረ።

በቡዶ ከሶ በዓል ላይ ተገኝተው የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት የአርባምንጭ ዙሪያ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አለማየሁ ዘይቴ በዓሉ አንድነትን የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

መንግስት በዓሉ ባህላዊ ይዘቱንና እሴቱን ጠብቆ እንዲከበር እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል ።

ከቁርሾና ጥላቻ ነፅተን በዓሉን ያለምንም ልዩነት ልናከብር ይገባል ያሉት አስተዳዳሪው በውይይትና በንግግር ችግሮችን ልንፈታ ይገባልም ሲሉ አሳስበዋል።

የዕለቱ የክብር እንግዳ የጋሞ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሪት አለሚቱ ዮሴፍ  “ለቡዶ ከሶ”  በዓል የእንኳ አደረሳችሁ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን ባህልን በመንከባከብ እና በመጠበቅ ለሁለንተናዊ እድገት የበኩላችንን  ማበርከት አለብን ነው ያሉት፡፡

በአዲሱ ዓመት አሮጌ አስተሳሰቦችን እና አመለካከቶችን በመተው በማህበራዊ ችግር ውስጥ ያሉትን በመርዳትና እርስ በእርስ ይቅር በመባባል መሆን አለበት ብለዋል።

በዞኑ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን የምናሳድግበትና እሴቶቻችንን የምናጎለብትበት ዘመን ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል።

የዘይሴ ብሔረሰብ ተወላጅ የሆኑት አቶ ገዛኸኝ ውንጉዳ እና አቶ እንግዳ እሳቱ ይህ ባህላዊ እሴት ለበርካታ ዘመናት ተጠብቆ መቆየቱን በዓሉን ያለልዩነት አንድ ሆነን የምንሻገርበት ነው ብለዋል ።

በዓሉ በተለያዩ ባህላዊ ስርዓቶች ታጅቦ በድምቀት ተከብሯል፡፡

ዘጋቢ ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባ ምንጭ