የቀቤና ልዩ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት በ2016 በጀት አመት አፈፃፀም ግምገማና በ2017 በጀት አመት ዋና ዋና ግቦች ዙሪያ የንቅናቄ መድረክ እያካሄደ ነው

ሀዋሳ፡ መስከረም 09/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቀቤና ልዩ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት በ2016 በጀት አመት አፈፃፀም ግምገማና በ2017 በጀት አመት ዋና ዋና ግቦች ዙሪያ የንቅናቄ መድረክ በወልቂጤ ከተማ እያካሄደ ይገኛል።

የንቅናቄ መድረኩ “የአመራርና የፈፃሚ አካላት ቁርጠኝነት፣ ተነሳሽነትና ተጠያቂነት በማረጋገጥ የህዝባችንን የጤና አገልግሎት ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት እናረጋግጣለን” በሚል መሪ ቃል ነው እየተካሄደ የሚገኘው፡፡

የቀቤና ልዩ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ አብድልኸይ ኑርሀሰን በንቅናቄ መድረኩ መክፈቻ ላይ እንደገለፁት፤ በሁሉም ደረጃ የተጠያቂነት አሰራር በመተግበር እንዲሁም የድጋፍና ክትትል ስራዎች ችግር ፈቺ እንዲሆኑ በማስቻል  የህዝቡን ሁሉ አቀፍ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚነትና ሽፋን ለማሳደግ ታልሞ የተዘጋጀ መድረክ ነው፡፡

ባለፈው በጀት ዓመት በጤናው ዘርፍ ያጋጠሙ ችግሮችን በመለየት በተያዘው የ2017 በጀት ዓመት የዘርፉን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል በትኩረት ይሰራል ብለዋል፡፡

ለዚህም የአመራርና የፈፃሚ አካላት ቁርጠኝነት፣ ተነሳሽነትና ተጠያቂነት ማጎልበት እንደሚገባ አቶ አብድልኸይ ተናግረዋል፡፡

በተጀመረው የጤና ጉባኤ የ2016 በጀት ዓመት በጤናው ዘርፍ የተከናወኑ አቤይት ተግባራት በዝርዝር ይገመገማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

መድረኩ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሲሆን በዛሬው ውሎ በተዘጋጀ ሰነድ ላይ የቡድን ውይይት እየተደረገ ይገኛል፡፡

በመድረኩ ላይ የክልሉ ባለድርሻ አካላት፣ የልዩ ወረዳው የዘርፉ አመራሮች እንዲሁም  የሁሉም የጤና  ተቋማት ኃላፊዎች እና ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው  ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ጅላሉ ፈድሉ – ከወልቂጤ ጣቢያችን