የ”ባለ ካዳቤ” በዓል የዕርቅ፣ የፍቅር፣ የአንድነትና የብርሃን ተምሳሌት መሆኑ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ መስከረም 08/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የጊዲቾ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ በዓል የዕርቅ፣ የፍቅር፣ የአንድነትና የብርሃን ተምሳሌት የሆነው “ባለ ካዳቤ” ከሌሎች ባህላዊ በዓላት ልዩ እንደሚያደርገው ተገለጸ።

የበዓሉን መድረስ የሚያበስሩ “ሶምቦሎልተ” ተብለው የሚጠሩ ወፎች ከሰሜን ወደ ደቡብ አቅጣጫ በረድፍ እየበረሩ የሚያልፉበት ነው።

በብሔረሰቡ ዘንድ ከሚከበሩ አደባባይ ባህላዊ በዓላት መካከል አውራ በዓል የሆነው “ባላካዳቤ” የተለያዩ ባህላዊ እሴቶችን በውስጡ ያቀፈ መሆኑ ተገልጿል።

ብርብር ከተማ አስተዳደር የብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ ስትሆን በዋናነት የጋሞ እና የጊዲቾ ብሔረሰብ መገኛ መሆኗን የተናገሩት የብርብር ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አብርሃም አይካ የጊዲቾ ብሔር ዘመን መለወጫ ባላ ካዳቤ በዓል ትልቅ ሥፍራ የሚሰጠው ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የመጣ መሆኑን ተናግረዋል።

የጋሞ ዞን አስተዳደር ጽ/ቤት ኃላፊ እና የአስተዳደር ተወካይ እንዲሁም የዕለቱ የክብር እንግዳ አቶ ማዶ መንገሻ እንዳሉት በጋሞ ዞን የሚገኙ ብሔረሰቦች የዘመን መለወጫ በዓል ዮ-ማስቃላ፣ ባላ ካዳቤና ቡዶ ኬሶ በየዓመቱ በተለያዩ ዝግጅቶች ይከበራሉ ብለዋል ።

የበዓሉ ታዳሚዎች በሰጡት አስተያየት የብሔረሰቡ ማንነት መገለጫ የሆነውን ባላ ካዳቤና ባህላዊ እሴቱን ከትውልድ ወደ ትውልድ ለማስተላለፍ ሁሉም የየድርሻውን መወጣት እንዳለበት አመላክተዋል።

ዘጋቢ: ሰለሞን አላሶ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን