“አንድነታችንን በማጎልበት የህዝብ ጥቅም የሚያስቀድም ፖለቲካ ማራመድ ይጠበቅብናል” ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ

“አንድነታችንን በማጎልበት የህዝብ ጥቅም የሚያስቀድም ፖለቲካ ማራመድ ይጠበቅብናል” ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ

ሀዋሳ: ሰኔ 24/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሠላም፣ የአንድነት እና የልማት ኮንፈረንስ መድረክ ሁለተኛ ቀን ውሎ የዕለቱ የክብር እንግዳ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ዋና ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ በተገኙበት እየተካሄደ ነው።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በዚህ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት ነጠላ ትርክትን በማስቀረትና ገዢ ትርክትን በመገንባት በጋራ በመሆን የህዝብ ጥቅም የሚያስቀድም ፖለቲካ ማራመድ ይገባል ብለዋል።

ያለፈው ጥሩ ያልሆነ ትውስታን በመተው ወንድማማችነትና መግባባትን በማጠናከር ለክልሉ ብልፅግና መትጋት እንደሚገባም እየተካሄደ በሚገኘው የሰላም፣ አንድነትና ልማት ጉባኤ ላይ ርዕሰ መስተዳድሩ ባስተላለፉት መልዕክት ጠቁመዋል።

በቀጣይ ኢ-ፍትሃዊ ተጠቃሚነትና የግል ጥቅምን ከማስቀደም ይልቅ አብሮነት ላይ በማተኮር የሰከነ ፖለቲካ እንዲረጋግጥ ብሎም ክልሉ የሰላም፣ የመቻቻል እና የብልጽግና ተምሳሌት ሆኖ እንዲቀጥል ሁሉም ኃላፊነቱ እንዲወጣ አሳስበዋል።

ክልሉ ከተመሰረተ በኋላ አዳጊና ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ቢመዘገቡም የሚያጋጥሙትን ጊዜያዊ ፈተና እና ችግሮችን በመሻገር የጉባኤው ተሳታፊዎች በሙያቸው የራሳቸውን አሻራ እንዲያስቀምጡ ጠይቀዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምስረታ ሂደት ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር ) እና በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ማስተባበሪያ ማዕከል ዋና ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ ላደረጉት ድጋፍም ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ምስጋና አቅርበዋል።

ዘጋቢ: ዘላለም ተስፋዬ