የተጣለበትን ኃላፊነት በመወጣት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየሠራ መሆኑን በጌዴኦ ዞን የቡሌ ወረዳ ምክር ቤት አስታወቀ

ምክር ቤቱ 4ኛ ዙር 30 መደበኛ ጉባኤውን አካሂዷል፡፡

በጉባኤው መክፈቻ የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ አቶ ዋቆ መኮና፤ ምክር ቤቱ የተጣለበትን የህዝብና የመንግሥት ኃላፊነት በአግባቡ በመወጣት የህብረተሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በወረዳው በ2016 ዓ.ም የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትን ሪፖርት ያቀረቡት የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ በራቆ በራሶ በግብርናው ዘርፍ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፤ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በሚደረገው ርብርብ ወረዳው ትልቁን ድርሻ በመውሰድ በትኩረት እየሠራ አንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

በወረዳው ለአርሶአደሩ በቂ የገብስና ድንች ምርጥ ዘር በማቅረብ ምርታማነት እንዲጨምር ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው እንዲያመርቱ በማድረግ የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ጠቁመዋል፡፡

በቡና እና በሌሎች ግብርና ዘርፎችም የአርሶአደሩን ተጠቃሚነት ሊያሻሽሉ የሚችሉ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል፡፡

የቡሌ ከተማን የንጹህ የመጠጥ ውሃ ችግር ለመፍታት በትኩረት እየተሠራ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡

በወረዳው መልካም አሰተዳደር እንዲሰፍን ለማድረግ ከተለያዩ አካላት የሚቀርቡ የመልካም አስተዳደር አቤቱታዎችን በመፍታት ለዘላቂ ተጠቃሚነት በትኩረት እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡

በትምህርት ዘርፍ የተስተዋለውን የውጤት መጥፋት ችግርን ተከትሎ ውጤት ለማሻሻል የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውንም በሪፖርቱ ገልጸዋል፡፡

በጤና ዘርፍ ከአካባቢው ንጽህና ጀምሮ የእናቶችንና የህጻናት የጤና አገልግሎት ላይ የተያዙ ዕቅዶችን በማከናወንና ህብረተሰቡ ማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድን አገልግሎት ተጠቃሚዎች እንዲሆን በማድረግ ረገድ በርካታ ሥራዎች ተሠርተዋል ነው ያሉት አስተዳዳሪው፡፡

በወረዳው ለተለያዩ ችግሮች የተጋለጡ ህጻናትን ለይቶ ድጋፍ በማድረግና ህገ ወጥ ዝውውር እንዳይፈፀም እየተሠራ እንደሆነም አቶ በራቆ ገልፀዋል፡፡

በምክር ቤቱ የተለያዩ ሪፖርቶች ለውይይት ቀርበው ይጸድቃሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ዘጋቢ፡ እምነት ሽፈራው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን