ማስተር አብነት ከበደ በጎፋ ዞን በመሬት መንሸራተት ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች ከ1 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የቁሳቁስ ድጋፍ አደረጉ

ድጋፉን የተረከቡት የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ ቅን ልብ ካላቸው ኢትዮጵያውያን መካከል አንዱ የሆኑት ማስተር አብነት፤ ኢትዮጵያዊነት ምን ማለት እንደሆነ በተግባር ያሳዩ የቁርጥ ቀን ልጃችን ናቸው ብለዋል።

ማስተር አብነት አደጋው ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ ክስተቱ ከኢትዮጵያ አልፎ በዓለምአቀፍ ደረጃ እንዲታወቅና ተጎጂዎች ሰብዓዊ ድጋፍ እንዲያገኙ በተለያዩ የሚዲያ አውታሮች በማሰራጨት የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ መቆየታቸውን ተናግረዋል።

ማስተር አብነት ለተጎጂዎች በራሳቸው ከሚያደርጓቸው ድጋፎች በተጨማሪ ኢትዮጵያውያንና በተለያዩ ዓለም ሀገራት የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ድጋፍ እንዲያደርጉ በማስተባበር ላሳዩት ኢትዮጵያዊነት በዞኑ አስተዳደርና በተጎጂ ቤተሰቦች ስም ኢንጂነር ዳግማዊ አመስግነዋል።

በዕለቱ የምስጋና ምስክር ወረቀት ከጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ እጅ ለማስተር አብነት ከበደ ተበርክቶላቸዋል።

ማስተር አብነት ድጋፉን ባስረከቡበት ወቅት፥ በደረሰው ድንገተኛ የመሬት መንሸራተት አደጋ በርካታ ዜጎች ሕይወታቸውን ማጣታቸውን ገልጸው፤ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን እንዲሁም ዓለምአቀፉ ማህበረሰብ ድጋፍ እንዲያደርጉ የበኩላቸውን ድርሻ ሲወጡ መቆየታቸውን ተናግረዋል።

በቀጣይ ተጎጂዎች በዘላቂነት እስኪቋቋሙ ድረስ የሚያደርጉትን ሰብዓዊና ቁሳዊ ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ማስተር አብነት ተናግረዋል።

ዘጋቢ: አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን