ሀዋሳ፡ መስከረም 04/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) አርሶ አደሩን ተጠቃሚነትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የኣሪ ዞን ግብርና መምሪያ ገለፀ፡፡
ዞኑ በደቡብ ኣሪ ወረዳ በ75 ሄክታር መሬት የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት አስጀምሯል ፡፡
የአርሶ አደሩን የምርጥ ዘር ችግር ለመቅረፍ የባለድርሻ አካላት ድጋፍ እንደሚያስፈልግ የገለፁት የደቡብ አሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግዛው ኃይሌ ለውጤታማነቱ ወረዳውም ክትትል እንደሚያደርግ ተናግረዋል ፡፡
የደቡብ አሪ ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዮሐንስ ማሚሶ እንደገለፁት የዘር ችግርን በዘላቂነት ለመፍታት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚችሉ የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት ሥራን አምና በ40 ሄክታር መሬት ዘንድሮ በ75 ሄክታር በማከናወን አርሶ አደሩ በምግብ ራሳቸውን እንዲችሉ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል፡፡
ለአከባቢው ስነምህዳር የሚስማማ የተሻለ ምርጥ ዘር በማፍለቅ ለማዕከላዊ ምርጥ ዘር ድርጅት ለማቅረብ እየተሠራ መሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፥ የአርሶአደሩን ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ታቅዶ እየተሠራ እንዳለም ገልፀዋል ፡፡
የአርሶአደሩን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የቴክኖሎጂ አማራጮችን በማስፋት በዞኑ ሁሉም ክላስተር ለስንዴ ምርት ትኩረት እንደሚሰጥም ተመላክቷል፡፡
በፕሮግራሙ የተሳተፉ አርሶአደሮች እንደገለፁት ቴክኖሎጂን በመጠቀም ምርታማነታቸውን ለማሳደግ በኩታ ገጠም በማረስ ጥሩ ምርት ለማግኘት ተግተው እንደሚሠሩ ተናግረዋል ፡፡
ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢየችን

More Stories
የአስተሳሰብና የተግባር አንድነት በማጠናከር ክልላዊ አንድነትን ማጎልበት እንደሚገባ ተገለጸ
ህዝበ ሙስሊሙ የመውሊድ በዓልን ሲያከብር በብዝሃነት ውስጥ የሚንፀባረቁ የመረዳዳትና የአብሮነት በጎ እሴቶችን ይበልጥ በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ኃላፊና የየዞን ከፍተኛ አመራሮች በሣውላ ማረሚያ ተቋም አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ