እደሁሌም ዘመንን ዘምን ሊተካው ወቅትም በጊዜ ቀመር ውስጥ ሊለወጥ ግድ ነው እና ‹‹አበባ አየሽ ወይ ለምለም›› ብለን ተቀብለነው የነበረው አዲስ ዓመት ለመሸኘት ቃላት እያሽሞነሞንን  ነው ፡፡

አዲስ 365 ቀናት ሊሰጡ ነው እነዚህን ቀናት ለመቀበል ከልጅ እስከአዋቂው እቅድ ማውጣቱ የተለመደ ነው ሁላችንም ጋር ግን እደክፍተት የምንወስደው ግን ያለፈው አመት እቅድ ወደኋላ መለስ ብለን የተሳካውን ያልተሳካውን ለመገምገም አለመነሳታች ነው ፡፡

እስቲ ስለ አዲስ ዓመት እቅድና ትግበራው የሰዎች እይታ ምንይመስል እንደሆነ በሀዋሳ ከተማ ተዟዙረን እንዳንዶችን አወራናቸው፡፡ አቶ ግዛቸው ጥላሁን ስለ አዲስ ዓመት እቅድ የሚከተለውን አስተያየት ሰጡን፤ እቅድ  ማቀድ መዘጋጀትን የሚጠይቅ ሁሌም ትጉህ ለመሆን ሲያግዝ በተቃራኒው አለማቀድ በዘፈቀደ ኑሮን እንድንኖር ያደርጋል።

አለማቀድ የስንፍና ምልክት ነው የሚሉት ሌላኛዋ የሀዋሳ ነዋሪ  ወ/ሮ ዘሪቱ ፍታአምላክ   ለማቀድ ትልቅ ነገር አያስፈልገንም ባለችን ነገር ተነሳሽነት ነገን በሰፊው እያዩ ለእቅዳችን ቅድሚያ በመስጠት መትጋት እንደሚገባ ገልጸውልናል።

እቅድ ለነገ ማንነት ወሳኝ ነገር በመሆኑ ማንም የት እደሚሄድ ሳያውቅ መንገድ እንደማይጀምር ሁሉ የትም አይደርስም  አዲሱ አመት በእቅድ መምራት መቻል እንደሚገባ አስተያየት ሰጪዎቹ ጠቁመዋል ።

እቅድ ማለት በቀላል አነጋገር አንድን ነገር ለማሳካት የሚደረግ ዝግጅት እንደሆነ የሚገልጹት በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስነ-ልቦና መምህሩ ወንድምአገኝ ግርማ እቅድ ሊፈጠሩ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሞ ለመለየት እና ለመፍታት እንደሚያስችል ይገልፃሉ።

አዲስ አመትን ከእቅድ ጋር በማያያዝ ስንመለከት በህይወታችን ውስጥ አዲስ ጅምር እና ለውጥ እንደሚያመጣ በግልፅ ማየት እንችላለን የሚሉት መምህር ወንድምአገኝ በየአመቱ የሚመጣው አዲስ አመት ለራሳችን አዲስ ግቦችን በማውጣት እና እነዚህን ግቦች ለማሳካት ዝርዝር እቅድ በማዘጋጀት አንድ ዓይነት አዲስ ምዕራፍ እንድንከፍት የሚያደርገን ልዩ አጋጣሚ ነው ሲሉ ያስረዳሉ።

የአዲስ አመት እቅድ አንድ ሰው በህይወቱ ውስጥ ለውጥ ለማምጣት የሚረዳና ህይወትን ለመምራት የሚጠቅም ሲሆን በአንጻሩ ደግሞ ማቀድ ብቻውን ግብ እንዳልሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ እቅድ ሲታቀድ የዕቅዱ መነሻ እንደሚኖረው ሁሉ እቅዱን ለመተግበር ደግሞ ጠንካራ ቁርጠኝነት እና ተግዳሮቶችን ተቋቁሞ ወጥነት ባለው መንገድ መፈጸም እንደሚያስፈልግ የስነልቦና መምህሩ ያሳስባሉ፡፡

ዘጋቢ : ቤተልሔም ለገሰ