ኢትዮጵያዊያን ከተባበርንና ከተጋገዝን ድህነትን ድል በማድረግ ብልፅግናን እንደምናመጣ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 04/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ኢትዮጵያዊያን ከተባበርንና ከተጋገዝን ድህነትን ድል በማድረግ ብልፅግናን እንደምናመጣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ገለጹ፡፡

ቢሮው “የኅብር ቀን” የሆነውን ጳጉሜን 4 በማስመልከት በአርባምንጭ ከተማ የአቅመ ደካማ ወገኖችን ቤት ግንባታ ማስጀመሪያ መርሀ ግብር አከናውኗል።

ዛሬ ጳጉሜን 4 – የኅብር ቀንን ምክንያት በማድረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ቢሮ የአካባቢውን ባለሀብቶች በማስተባበር በከተማው የአቅመ ደካማ ወገኖችን ቤት ማስገንባት የሚያስችል ማስጀመሪያ መርሀ ግብር ተከናውኗል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በመርሀ ግብሩ እንዳሉት የዛሬውን የኅብር ቀን በማስመልከት የአቅመ ደካማ ወገኖች በተሻለ ቤት እንዲኖሩ እያገዝን እንገኛለን።

የጋሞ ዞን አስተዳዳሪ አቶ አባይነህ አበራ ዛሬ በአርባምንጭ ከተማ ለአቅመ ደካማ ወገኖች የተደረገው ድጋፍ የህብረ ብሔራዊነታችን ማሳያ በመሆኑ የክልሉ ስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ቢሮ ሊመሰገን ይገባል ሲሉ ገልፀዋል።

ለአቅመ ደካሞች የተሻለ መጠለያ ለመገንባት ቅድመ ዝግጅት ማድረጋቸውን የጠቆሙት ግንባታውን ከሚያደርጉ የከተማው ባለሀብቶች መካከል አቶ አለማየው ካሳ፤ ከ2 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ በማውጣት በአነስተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙትን ወገኖች ቤት ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ተናግረዋል።

ድጋፍ ከተደረገላቸው መካከል ወ/ሮ ዘነበች ነጋሽ እና ወ/ሮ አዳነች ብሩ በተደረገላቸው ድጋፍ መደሰታቸውን ተናግረው ስለተደረገላቸው ድጋፍ አመስግነዋል።

ዘጋቢ፡ ተመኙህ ገረሱ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን