መተጋገዝ፣ መተባበርና መቀናጀት ሀገርን ይቀይራል ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ አስታወቀ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 04/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) መተጋገዝ፣ መተባበርና መቀናጀት ሀገርን ይቀይራል ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ አስታውቋል።

የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ድርጅት ጂንካ ቅርንጫፍ አመራርና ሠራተኞች ጳጉሜ 4 የህብር ቀንን “የብሔራዊነት ተምሳሌት” በሚል መሪ ቃል በተለያዩ በጎ ተግባራት አክብሯል።

የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ድርጅት ጂንካ ቅርንጫፍ ሥራ አስክያጅ አቶ ሙሉዋስ አትሳ በንግግራቸው የህብረ ብሔራዊነት ምሳሌ ወደ ሆነችው ደቡብ ሬዲዮ እንኳን ደህና መጣችሁ ካሉ በኃላ አነስተኛ የገቢ ምንጭ ያላቸው ሠራተኞን በተቋሙ ሠራተኞች መዋጮ በመደገፍ በዓልን ያለ ሃሳብ እንዲያከብሩ ለልጆቻቸው የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል።

የኣሪ ዞን አሰተዳደር ተወካይ አቶ ይሄነው ተሰፋዬ ተቋሙ ዛሬ የሚከበረውን ቀን የሚገልጽ ህብረት ያሳየ በመሆኑ አመስግነው በዘንድሮ ክረምት በርካታ በጎ ተግባር መከወኑን ገልፀው የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ሠራተኞች ያሳዩት በጎ ተግባር ለሌሎች አርአያ እንደሆነ ገልፀዋል።

የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ድርጅት መልካም ነገር የሆነውን ተግባር ለማከናወን ህብረት መፍጠራቸው የሚያስመሰግን ነው ያሉት ደግሞ የጂንካ አጠቃላይ ሆስፒታል ሥራ አስክያጅ ታጋይ ሳህለ ናቸው።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትል ኃላፊና የወጣቶች ዘርፍ ኃላፊ አቶ ማርቆስ ማትዮስ እንደ ክልል በበጎ ተግባር በአንድ ጀንበር 3 ሺህ ቤት ለመገንባት ታቅዶ 4 ሺህ 700 በላይ  ቤት መገንባት መቻሉንና ሌሎችም በጎ ተግባራት ያለ ምንም ክፍያ ተግባራቱ ትኩረት እንዲያገኙ እስከ ቀበሌ በመውረድ ላሳዩት ሙያዊ ኃላፈነት ምስጋና አቅርበዋል።

 በመሆኑም መተጋገዝ መተባበርና መቀናጀት ሀገርን የሚቀይር እንደ መሆኑ በዚህ ልክ በክልላችንም የበጎ ምግባር ተግባራት ባህል እየሆነ መምጣቱን ያሳያል ብለዋል።

ለጂንካ አጠቃላይ ሆስፒታል የማሽን ግዥ ለሚደረገው ንቅናቄም የወር ደሞዛቸውን በመለገስ የንቅናቄው አካል እንደሚሆኑም አቶ ማርቆስ ገልፀዋል።

በዕለቱ አነሰተኛ ገቢ ላላቸው የተቋሙ ሠራተኞች ለልጆቻቸው የሚሆን ደብተርና ስክሪብቶ ድጋፍ የተደረገ ሲሆን በተቋም ደረጃም ለጂንካ ሆስፒታል ማሽን የብር ድጋፍ ማድረጋቸውንና በቀጣይም ድጋፋቸውን እንደሚያጠናክሩ ተገልጿል።

ድጋፍ የተደረገላቸው የተቋሙ ሠራተኞችም በተደረገው ድጋፍ ደሰተኛ መሆናቸውንና የተቋሙን አጠቃላይ ሰራተኛና አመራሩን አመስግነዋል።

ዘጋቢ: ከተማ በየነ – ከጂንካ ጣቢያችን