ጳጉሜን 4 የኅብር ቀን በጌዴኦ ዞን በዲላ ከተማ ተከበረ

“ኅብራችን ለሰላማችን” በሚል መሪ ቃል ነው ጳጉሜን 4 – የኅብር ቀን የተከበረው።

የፕሮግራሙ መክፈቻ የተለያዩ ስፖርታዊ ትርዒቶች፣ በባህላዊና በዘመናዊ ውዝዋዜ በደመቀ ሁኔታ ተከብሯል፡፡

ከልዩ ልዩ ዝግጅት በኋላ በተካሄደው በፓናል ውይይት መድረክ የመክፈቻ መልዕክት ያስተላለፉት የጌዴኦ ዞን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ዜና ማሞ፣ የህብር ቀን ስናከብር ባለብዙ መልክ የሆነችውን ኢትዮጵያን ለማጽናት የሚከፋፍሉ ትርክቶች ከማጉላት ህብረ ብሔራዊ አንድነታችንን በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ማትኮር መቻል አለብን ብለዋል፡፡

ብዙ ሆነን አንድ፤ አንድ ሆነን ብዙ በመሆን የተገኘውን የሀገራችንን የአብሮነት እሴት በማድመቅ ዘላቂ ሠላም ማስፈንና ሀገረ መንግሥት መገንባት አለብን ብለዋል ወ/ሮ ዜና፡፡

የዞኑ ብልጽግና ፓርቲ የፖለቲካና ርዕዮተ አለም እና የህዝብ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ተስፋጽዮን ዳካ፤ አሮጌውን አመት በብዙ ፈተናዎች ውስጥ ሆነን በጉልህ ስኬቶች በማለፍ ለዛሬው ቀን መድረሳችንን ተናግረዋል፡፡

በአዲሱ አመት የህብረ ብሔራዊ አንድነትን በማጠናከር የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን በድል በማሸነፍ ልማትና ሠላም ለማስፈን ሁላችንም በትጋትና በጽናት መስራት ይኖርብናል ብለዋል፡፡

በመርሃግብሩ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዲላ ክላስተር ቢሮ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች፣ የዞን፣ የዲላ ከተማ፣ የዲላ ዙሪያ ወረዳ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የፀጥታ አካላት እና ነዋሪዎች ተሳትፈዋል፡፡

ዘጋቢ፡ እምነት ሽፈራው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን