ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተሰራው ሁሉ አቀፍ ተግባር አመርቂ ውጤት ማስገኘቱ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 03/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተሰራው ሁሉ አቀፍ ተግባር አመርቂ ውጤት ማስገኘቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት አስታወቀ፡፡

የክልሉ የምግብ ስርዓትና የስነ ምግብ ም/ቤት በአርባ ምንጭ ከተማ የምክክር መድረክ አካሂዷል።

የዜጎችን የአመጋገብ ስርአት በማዘመን የመቀንጨር ችግርን ለማስወገድ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድሩ ልዩ አማካሪ ዶ/ር ብርሃኑ ጌቦ በክልሉ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጥረቶች መደረጋቸውን ተናግረው በዚህም ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውንም አስታውሰዋል።

የእናቶች፣ የህፃናትና የወጣቶችን ሥርአተ ምግብ በማሻሻል አምራችና ጤናማ ዜጋን መፍጠር እንደሚያስፈልግም ዶ/ር ብርሃኑ አውስተዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት በአዲስ መልክ ከተደራጀ  ጀምሮ የክልሉን ህዝብ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር ጥረቶች መደረጋቸውን ያስታወሱት ዶ/ር ብርሃኑ በዘርፉም አመርቂ ውጤት መመዝገቡንም ተናግረዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግስት የምግብ ስርአትና ኒውትሬሽን ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ ተሻለ ማናዬ በበኩላቸው በክልሉ በሥነ ምግብና ተያያዥ ጉዳዮች ምክንያት ሊከሰቱ የሚችሉ ችግሮችን መሠረት አድርጎ የተቋቋመው ም/ቤት በርካታ ተግባራትን እያከናወነ መቆየቱን አስታውሰዋል።

ጤንነቱ የተጠበቀ ባለብሩህ አዕምሮ ባለቤት የሆነ ትውልድ ይኖር ዘንድ የተመጣጠነና ደህንነቱ የተጠበቀ ሥርአተ ምግብ ያስፈልጋል ያሉት አቶ ተሻለ ለዚህም ባለ ድርሻ አካላት ተሳትፎ ወሳኝ ነውም ብለዋል።

በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ልዩ ትኩረት ተሠጥቶት እየተሠራበት ያለው የምግብ ስርዓትና ኒውትሬሽን ም/ቤት ማነቃቂያ መድረክ ላይ ከክልሉ የተወጣጡ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።

ዘጋቢ፡ በኃይሉ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን