የንግዱን ሥራ የተቀላጠፈ ለማድረግ ነጋዴውን ማህበረሰብ ማገዝ እንደሚገባ ተገለጸ

ሃዋሳ፡ ጳጉሜ 03/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የንግዱን ሥራ የተቀላጠፈ ለማድረግ ነጋዴውን ማህበረሰብ የማገዝ ስራ እንደሚሠራ የደቡብ ኢትዮጵያ ንግድ ማህበራት ገለፀ።

ማህበሩ በክልሉ የሚገኙ ነጋዴዎች ራሳቸውን የነቃ ነጋዴ በማድረግ ልምድ ማካበት እንዲችሉ ከኢንዶኔዥያ መንግስት ጋር እየሠራ መሆኑን አመላክቷል።

ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተወጣጡ ባለሀብቶች በውይይት መድረኩ የተገኙ ሲሆኑ በተለይም የኢንዶኔዥያ አምባሳደር በንግድ ሂደቱ ዙሪያ ሰፊ ልምድ አካፍለዋል።

በዋናነት ደግሞ በኢንዶነዢያ ጥቅምት መጀመሪያ ላይ በሚደረገው የንግድ ኤክስፖ በመሳተፍ ልምድ ማካበት እንዲችሉ አምባሳደሩ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

በሌላ መልኩ ኢንዶኔዥያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት የሁለትዮሽ ግንኙነት በመጠቀም ምን ያክል ኢኮኖሚዋን እንዳሳደገች ለባለሀብቶች እና ለመንግስት የሥራ ኃላፊዎች ቀርቧል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የንግድ ማህበራት ፕሬዚዳንት አቶ ቦጋለ ቢታኔ መድረኩ በዋናነት ነጋዴው ማህበሰብ ከባህላዊ የንግድ ሥርዓት በመላቀቅ አቅሙን አሳድጎና አዘምኖ አስመጪና ላኪ መሆን እንዲችል ታስቦ መዘጋጀቱን አመላክተዋል።

የኢንዶኔዥያው አምባሳደር በመድረኩ መገኘታቸው ኢንዶኔዥያ ላይ በሚካሄደው የንግድ ኤክስፖ የክልሉ ነጋዴዎችና ባለሀብቶች በመገኘትና ልምድ በመውሰድ አሰራራቸውን በመፈተሽና በማረም አስመጪና ላኪ ለመሆን እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል አቶ ቦጋለ።

ሌሎችም ባለሀብቶች ከእኛ ጋር በመሆን መስራት እንዲችሉ ጥሪ አስተላልፈዋል።

የዳሽን ባንክ የወላይታ ዲስትሪክት ዳይሬክተር አቶ ታዲዮስ ተስፋዬ ባለሀብቶች በዚህ መልክ ከንግድ አሰራሩ ጋር በተያያዘ የልምድ ልውውጥ ማድረግ መቻላቸው ከባህላዊ የንግድ አሰራር እንዲወጡ የሚያግዝ ነው ብለዋል።

በቀጣይም በዚሁ መድረክ የተገኙ ባለሀብቶች ኢንዶኔዥያ ላይ በሚካሄደው የንግድ ኤክስፖ ይገኛሉ ተብሎም እንደሚጠበቅ ለማወቅ ተችሏል ።

ዘጋቢ ፡ ታምሩ በልሁ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን