ለሕብረተሰቡ ልማትና መልካም አስተዳደር ጉዳዮች ትኩረት በመስጠት አበረታች ለውጦች መመዝገቡ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 03/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ለሕብረተሰቡ የልማት መልካም አሰተዳደር ጉዳዮች ትኩረት በመስጠት አበረታች  ለውጦች መመዝገባቸውን የይርጋጨፌ ወረዳ ምክር ቤት አሰታወቀ፡፡

ምክር ቤቱ 4ኛ ዙር 28 ኛ መደበኛ ጉባኤ  አካሂዷል።

በጉባኤው የመክፈቻ  ንግግር  ያደረጉት የወረዳው ም/ቤት ዋና አፌ ጉባኤ ወ/ሮ ናዝሬት ዘኪዮስ፥ በወረዳው የማህበረሰቡን የልማትና የመልካም አሰተዳደር ችግሮችን ትኩረት በመስጠት በግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ፣ በትምህርት፣   በመሠረተ ልማት በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን አመላክተዋል።

የወረዳው አሰተዳዳሪ አቶ ተሰፋዬ ሚጅ የ2016  በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም ሪፓርት አቅርበው  ውይይት የተደረገ ሲሆን በልማትና በመልካም አሰተዳደር ጉዳዮች ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውንና ሶስት ትላልቅ ፕሮጀክቾችን ማስመረቃቸውን ተናግረዋል።

በበጀት ዓመቱ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ፣ በጤና፣ በግብርና፣ በገቢ አፈፃፀም፣ በመሠረተ ልማትና እንደዚህም ለዘመናት ጥያቄ የሆነውን የወጣቶች ሰብዕና ማዕከል በመገንባት በርካታ የልማት ሰራዎችን በመፈጸም፣ የሕዝቡን ጥያቄ መመለሰ መቻላቸውን አንሰተው በቀጣይ በ2017 በጀት ዓመት የትምህርትን ስብራት በመጠገን ጤናንና አገልግሎትን ተደራሽ  በማድረግ  አጠናክረው  እንደሚሠሩ አብራርተዋል።

የምክር ቤት አባላትም በበጀት ዓመቱ የዘመናት ጥያቄ  የነበሩ የልማትና የመልካም አሰተዳደር ችግሮች የተመለሠበትና ትላልቅ ፕሮጀክቶች  ተመርቀው  ለአገልግሎት በመብቃታቸው መደሰታቸውን ገልፀዋል።

በቀጣይም የውስጥ ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ የልማት ውጥኖች በማጠናከር፣ የትምህርትን ሰብራት ለመጠገን፣ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦትና ምርታማነትን በማሳደግ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ እንደ ምክር ቤት አባል ተቀናጅተው እንደሚሠሩ አመላክተዋል።

ለ2017 ሥራ ዘመን የሚውል 476 ሚሊየን 791 ሺህ 423 ብር በጀት በሙሉ ድምፅ የፀደቀ ሲሆን በጀቱ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የምክር ቤቱ አባላት በአጽንኦት አሳስበዋል።

 ዘጋቢ : ጽጌ ደምሴ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን