በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ የሴት ልማት ህብረቶችን ሪፎርም በማድረግ የተሻለ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ መቻሉን የክልሉ ሴቶችና ህፃናት ጉዳይ ቢሮ ገለጸ።

ጳጉሜ 2 የሪፎርም ቀንን አስመልክቶ የቢሮው ምክትል ኃላፊና የሴቶች ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሪት ኩሪባቸው ታንቱ በሰጡት ማብራሪያ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ  ባገባደድነው 2016 ዓ.ም ሁሉንም የሴት አደረጃጀቶች ሪፎርም በማድረግ የተሻለ ውጤት የተመዘገገበት ነው ብለዋል።

በተደረገው ሪፎርም ከ1ሺህ በላይ የቁጠባና ብድር ህብረት ስራ ማህበራትንና 40 ሺህ 4መቶ 75  በኩታ ገጠም 30 አባላትን የያዙ የሴቶች ልማት ህብረቶችን ማደራጀት መቻሉን ገልጸዋል።

ጠንካራ የኢኮኖሚ አቅም ያላቸውን የሴት አደረጃጀቶች ከመፍጠር ጎን ለጎን በትምህርት፣በጤናና በሌሎችም ማህበራዊ ዘርፎች ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ወ/ሪት ኩሪባቸው ገልጸዋል።

ከጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች በዋናነት በሴት ልጅ ግርዛትና ያለ እድሜ ጋብቻን ቀድሞ ከመከላከል እና ጥቃቱን የፈጸሙ አካላትን ለህግ አቅርቦ ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኙ ከማድረግ ረገድ ይበል የሚያሰኝ ለውጥ መታየቱንም ተናግረዋል።

ዘጋቢ:- አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን