በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ ከ40 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ

ሀዋሳ፣ ጳጉሜ 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ወረዳ ከ40 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀዋል።

በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ተስፋዬ ሚጁ ከዚህ ቀደም የህብረተሰቡ የልማት ጥያቄዎች ከንግግር ባለፈ በተግባር ባለመመለሱ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች ሲዳረግ መቆየቱን ጠቁመዋል።

ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ህብረተሰቡን፣ መንግሥትንና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትን በማሳተፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ ከ40 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስተዳዳሪው ገልፀዋል።

የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶክተር ዝናቡ ወልዴ በበኩላቸው የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነትን ይበልጥ ለማረጋገጥ የይርጋጨፌ ወረዳ ማህበረሰብ ከመንግሥት አካላት ጋር በቅንጅት እያደረገ ያለው ተሳትፎ የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል።

የወጣቱ ትውልድ ስብዕና ተገንብቶ ለሀገር ልማት የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ በየደረጃው ያሉ አካላት ሁለተናዊ ድጋፍና እገዛ ማድረግ እንደሚገባ ዶክተር ዝናቡ አሳስበዋል።

በምረቃው መርሃ ግብር ላይ የተገኙ ወጣቶች እንዳሉት ከዚህ ቀደም መዝናኛ ቦታ አጥተው ለተለያዩ ችግሮች ሲዳረጉ መቆየታቸውን ተናግረው፤ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁ ተቋማት ችግሩን እንደሚቀርፍላቸው ተናግረዋል።

በህብረተሰቡና በመንግሥት ተሳትፎ ከተገነቡ ፕሮጀክቶች መካከል የወጣቶች መዝናኛ ማዕከል፣ የማር ማከማቻና ማቀነባበሪያ ማዕከላት ይገኙበታል።

ዘጋቢ፡ ዘርሁን ሹፌር – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን