በጌዴኦ ልማት ማህበር ከ13.6 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የወናጎ ወረዳ ባንቆ ኦኮቶ አንደኛ ደረጃ ት/ቤት ተመረቀ

ልማት ማህበሩ ከመንግስት ጎን በመሆን የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡

ማህበሩ ባለፉት ስድስት ወራት ገንብቶ ያጠናቀቀውን የወናጎ ወረዳ ባንቆ ኦኮቶ አንደኛ ደረጃ ት/ቤት የክልል፣ የዞን፣ የወረዳና ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዛሬው ዕለት አስመርቋል፡፡

ትምህርት ቤቱን ገንብቶ ለመጨረስ ስድስት ወራት ብቻ መፍጀቱን የገለጹት የጌዴኦ ልማት ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ብዙነህ ንጉሴ ግንባታውም ከ13.6 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የወጣበት ስለመሆኑም አብራርተዋል፡፡

የጌዴኦ ልማት ማህበር ምክትል ቦርድ ሰብሳቢና የዲላ ዩኒቨርሲት መምህር እና ተመራማሪ ረዳት ፕሮፌሰር ተስፋኖ በቀለ በበኩላቸው ማህበሩ ምንም እንኳን በራሱ የሚያመነጨው የገቢ አማራጮች የሌሉት ቢሆንም ከህብረተሰቡ የሚሰበሰበውን ውስን ሀብት በአግባቡና በጥንቃቄ በመጠቀም መንግስት መሸፈን ያልቻለውን የህብረተሰብ አንገብጋቢ ችግር በመለየት መፍትሔ እየሰጠ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳደር ዶ/ር ዝናቡ ወልዴ እንደሀገር የመሻገር ቀን እየተከበረ ባለበት ወቅት የተመረቀው ይህ ፕሮጀክት ከትምህርት ስብራት ችግር ተሻግረን የነገ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ወደማፍራት ምዕራፍ መሸጋገራችንን ያረጋገጥንበት ዕለት በመሆኑ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል፡፡

አክለውም ልማት ማህበሩ በቀጣይ በትምህርት፣ በጤና፣ በግብርናና ሌሎች መስኮች ለመስራት የወጠናቸውን ዕቅዶች ከዳር እንዲያደርስ ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበው ዞኑም በሙሉ አቅሙ ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጧል፡፡

ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን