የኤችአይቪ ኤድስ ስርጭትን ለመግታት ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ ይገባል – የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ጤና ቢሮ

ሀዋሳ፣ ጳጉሜ 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የኤችአይቪ ኤድስ ስርጭትን ለመግታት ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ጤና ቢሮ አሳሰበ።

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ጤና ቢሮ የኤች አይቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር ዳይሬክቶሬት የ2016 ዓ.ም አፈፃፀም ግምገማ እና የ2017 ዓ.ም ዕቅድ ዙሪያ የምክክር መድረክ በሚዛን አማን ከተማ አካሂዷል፡፡

የክልሉ ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም እንደገለፁት የኤችአይቪ ኤድስን ጨምሮ የሌሎች ተላላፊ በሽታዎችን ሥርጭት ለመግታት የክልሉ ጤና ቢሮ ከአጋር ድርጅቶች ጋር በቅንጅት ሲሰራ ቆይቷል።

በተለይም በክልሉ የኤችአይቪ ኤድስ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችሉ ግንዛቤ የመፍጠር ስራዎች በልዩ ትኩረት መከናወናቸዉን ገልፀዋል።

በክልሉ የኤችአይቪ ኤድስ ተጋላጭን ከመቀነስ አንፃር ባለድርሻ አካላት ቅንጅት እና ድጋፍ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል ኃላፊው።

የክልሉ ጤና ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ሀይሌ ዘውዴ በበኩላቸው የኤችአይቪ ኤድስ በሽታ በመከላከል እና መቆጣጠር በኩል በክልሉ ሁሉም ዞኖች እና ከተማ አስተዳደሮች የማህበረሰብ ንቅናቄ በመፍጠር ውጤታማ ተግባራት በተጠናቀቀው በጀት አመት ማከናወን መቻሉን አስረድተዋል።

የበሽታውን ሥርጭትን ለመግታት የሚያስችሉ የምርመራና የልየታ ተግባራትን ጨምሮ ቫይረሱ በደማቸው የተገኘባቸውን ወገኖች የፀረ ኤድስ ህክምና ማስጀመርና በዘላቂነት ማቋቋም ተግባራትም ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተከናወነ መሆኑን የጠቀሱት ምክትል ኃላፊዉ በ2017 በጀት አመትም ቅንጅታዊ አሰራሮችን በማጠናከር የበሽታዉን ሥርጭት በመግታት በኩል ትኩረት ተሰጥቶ ይሰራል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ዮሐንስ አሰፋ – ከሚዛን ጣቢያችን