በክልሉ የተመዘገበውን ውጤት ይበልጥ ማሳደግ ይገባል – አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር

ሀዋሳ: ጳጉሜ 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተመሰረተ ወዲያ በሁሉም ዘርፎች ያስመዘገበውን አበረታች ውጤት ይበል ማስቀጠል እንደሚገባ የኢፌዲሪ ፌደሬሽን ምክር ቤት አፈ አቶ አገኘሁ ተሻገር ገለፁ::

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል “ከአዲስ ምዕራፍ በወል እሴት ወደ መስፈንጠር” በሚል መሪ ቃል አንደኛ አመት የምሥረታ በዓሉን አክብሯል::

በክብረ በዓሉ ላይ የተገኙት የፌደሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ አገኘሁ ተሻገር፤ የፌደሬሽን ምክር ቤት ብሄር ብሄረሰቦች ማንነታቸው እንዲከበር በህግ የተቀመጠውን መብት የመፈፀም ሀላፊነት የተጣለበት ተቋም መሆኑን ገልጸዋል::

ኢትዮጵያ የበርካታ ማንነቶች ሀገር ናት ያሉት አፈ ጉባኤው፤ ህገ መንግስታችን የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች እራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ ይፈቅዳል ብለዋል::

ይሁንና ይህን ተግባራዊ ከማድረግ አኳያ እስከለውጡ ዋዜማ ድረስ ችግሮች እንደነበሩ አስታውሰዋል::

የለውጡ መንግስት ከወሰናቸው እና ምላሽ ከሰጠባቸው ወሳኝ ጉዳዮች መካከል በቀድሞ የደቡብ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ህዝብ ዘንድ ይነሱ የነበሩ የክልል መዋቅር ጥያቄዎች ምላሽ ማግኘታቸውን ተናግረዋል::

ከምሥታው ጀምሮ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልን ለመሩት ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው እና ለክልሉ አመራሮች ምስጋና አቅርበዋል::

“አሁን ክልሉ ጥሩ ሁኔታ ላይ ነው ያለው:: ጥሩ የአመራር ቅንጅት አለ::” ሲሉ የተናገሩት አቶ አገኘሁ ተሻገር በክልሉ በግብርናው ዘርፍ በ30:40:30 ፕሮግራም የመጣውን ውጤት ይበልጥ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል::

ግቡ ክልል መመሥረት አይደለም፤ ልማትን ማምጣት እንጂ ሲሉም ተናግረዋል::

“የክልሉ ህዝብ እና ምሁራን አመራሩን ሊያግዙ ይገባል:: የመዋቅር ጥያቄ ተመልሷል:: አሁን አመራሩ ልማት ላይ እንዲያተኩር ጊዜ መስጠት ያስፈልጋልም::” ነው ያሉት::

ለእኛ ባይሆንም ለልጆቻችን የምትመች ሀገር ሰርተን ማስረከብ እንደሚገባ ያሳሰቡት አፈ ጉባኤው የፌደራል መንግስትም ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል::

ዘጋቢ፡ ማሬ ቃጦ