“የመሻገር ጥሪቶች፤ የአዲስ ብርሃን ወረቶች” በሚል መሪ ቃል በኮሬ ዞንና ኬሌ ከተማ አስተዳደር በጋራ የፓናል ውይይት ተካሄደ

ውይይቱን በንግግር የከፈቱት የኬሌ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዮሐንስ ኃይሉ፤ የመሻገር ውጤቶች እየታዩ እንደሆነ በመግለጽ ከንግግር ባለፈ ሁሉም በተግባር በርትቶ መሥራት ይጠበቅበታል ብለዋል።

በኮሬ ዞን የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ጢሞቲዎስ በቀለ ያለን የተፈጥሮ ፀጋና ቀደምት አባቶች በጣሉልን መሠረት ላይ ቆመን ወቅቱን በመገንዘብ በጋራ በመተባበር ከተማን ማሻገርና አገርን ማሳደግ እንችላለን በማለት ተናግረዋል።

የኮሬ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ታረቀኝ በቀለ ውይይቱ 5ኛ ዙር የህዳሴ ግድብ ውኃ ሙሌት በተካሄደበት ማግሥት መሆኑ የተለየ እንደሚያደርገው በመግለጽ በሠላም ጊዜ ሠላም በመሥራት ከሰው ሠራሽ አደጋ ራሳችንን በመጠበቅ እየታየ ያለውን ብሩህ ተስፋ ከዳር እናደርሳለን ብለዋል።

ከተሳታፊዎች አቶ ምትኩ ኩራዝ፣ መምህር አርጋው ጥላሁንና ሌሎች በሰጡት አስተያየት በበርካታ ችግሮች መካከል በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን በማንሳት ያለንን በመንከባከብ፣ ቀሪውን በብርታት መሥራት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።

አክለውም ልማት፣ ሠላምና ማህበራዊ ጉዳዮች ለተወሰኑ አካላት የሚተው ባለመሆናቸው በአንድነትና በብርታት መሥራት እንደሚጠይቅ አስታውሰዋል።

በፓናል ውይይቱ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች እና የመንግሥት ሠራተኞች ተሳተፈዋል።

ዘጋቢ: ምርጫ መላኩ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን