“የመሻገር ጥሪቶች፤ የአዲስ ብርሃን ወረቶች” በሚል መሪ ቃል የመሻገር ቀን በተለያዩ ዝግጅቶች በአርባ ምንጭ ተከበረ

ሀዋሳ፡ ጳጉሜ 01/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) “የመሻገር ጥሪቶች፤ የአዲስ ብርሃን ወረቶች” በሚል መሪ ቃል የጋሞ ዞን፣ የአርባ ምንጭ ከተማ አስተዳደርና በአርባ ምንጭ ማዕከል የሚገኙ የክልል ቢሮዎች የመሻገር ቀንን በተለያዩ ዝግጅቶች አክብረዋል።

የጋሞ ዞን ዋና የመንግሥት ተጠሪ አቶ ሰብስቤ እየተመዘገቡ ያሉ ለውጦችን ለማስቀጠል በአዲሱ አመት አዲስ ተስፋ ሰንቀን መሥራት ይጠበቅብናል ብለዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ፤ የ2016 ዓ.ም የክልሉ ሕዝቦች ራስን በራስ ለማስተዳደር በፍላጎታቸው የመደራጀት ይሁንታ ያገኙበት፣ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች እና ሌሎች የልማት ትሩፋቶች የተመዘገቡበት ዓመት እንደሆነ አስታውሰው በመጪው ዓመት ለልማት የተነቃቃውን የክልሉን ሕዝብ ይዘን ከሠራን ሰፊ የመልማት ዕድል በእጃችን አለ በማለት ተናግረዋል።

በተሠማራንበት መስክ ሁሉ ለአገር ግንባታ ተስፋ ሰንቀን በትጋት መሥራት ይጠበቅብናል ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ፤ የምንቀበለው አዲሱ ዓመት የተስፋ ብርሃን የምንሰንቅበት እንዲሆንም ተመኝተዋል።

በመሻገር ቀን የአርባ ምንጭ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክት የሥራ እንቅስቃሴ እና ሌሎች የልማት ድርጅቶች በተሣታፊዎች ተጎብኝተዋል።

ዘጋቢ: ወ/ገብርኤል ላቀው – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን