የሪፎርም ስራ ተቋማት ከተገልጋዩ ህብረተሰብ ለሚነሱ የልማትና መልካም አስተዳደር ችግሮች ምላሽ ለመስጠትና የአገልግሎት አሰጣጣቸውን ለማዘመን እንደሚያግዝ ተገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 30/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የሪፎርም ስራ ተቋማት ከተገልጋዩ ህብረተሰብ ለሚነሱ የልማትና መልካም አስተዳደር ችግሮች ምላሽ ለመስጠትና የአገልግሎት አሰጣጣቸውን ለማዘመን ያግዛል ሲሉ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የውሃ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ዳዊት ሀይሉ ገለጹ።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሃ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ በተቋም ተኮር የሪፎርም መሣሪያዎች አተገባበር እና በዲስፕሊን መመሪያ ዙሪያ ለቢሮው ሠራተኞች የተዘጋጀ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና መድረክ በወልቂጤ ከተማ እየተሰጠ ይገኛል።

ስልጠናው ከክልሉ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ጋር በመተባበር የተዘጋጀ የአቅም ግንባታ ስልጠና መሆኑም ተጠቁሟል።

የስልጠና መድረኩን በንግግር የከፈቱት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሃ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ዳዊት ሀይሉ እንዳሉት ስልጠናው የክልሉ መንግስት የመልካም አሰተዳደርና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመፍታት ሰፊ ንቅናቄ ለማድረግ እና ጳጉሜ 2 የሪፎርም ቀን በሚል ልዩ ትኩረት በመስጠት ሁሉም የመንግስት ሠራተኛ መደበኛ ስራ ላይ እንዲገኝ እንደ ሀገር ከተቀመጠ አቅጣጫ በፊት መደረጉ ልዩ ያደርገዋል።

የሪፎርም ስራ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጣቸውን እንዲያዘምኑ ያግዛል ያሉት አቶ ዳዊት ከዚህ ቀደም ሲደረግ የነበረውን የሪፎርም ስራ ማስተግበሪያ መመሪያ በመስጠት እንደነበርና አሁን ግን ወደሴክተር ተኮር የሪፎርም ትግበራ ምዕራፍ መሸጋገር መቻሉን በንግግራቸው አንስተዋል።

የሪፎርም ሂደቱም በተለይ ጤናማ የቡድን ስሜት ከመንገባት፣ የውጤት ተኮር ስራን በተሟላና ውጤታማ በሆነ መልኩ ለመተግበር የተሻለ ግንዛቤ የሚፈጠርበት ስልጠና መሆን እንዳለበት ገልፀዋል።

በስልጠናው ወቅት በዋና ዋና ዘርፎች በተለይ ከጥናትና ዲዛይን ጥራት መጓደል፣ በግንባታ ክትትልና ቁጥጥር፣ በግንባታ ሂደት ላይ የሚያስከትላቸው ጫናዎችን መለየትና የፈፃሚውን አቅም መገንባት ያስፈልጋል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ተዘራ በቀለ – ከወልቂጤ ጣቢያችን