ምክር ቤቱ ከህዝብና መንግሥት የተጣለበትን ኃላፊነት በሚገባ በመወጣት የህዝቡን ጥያቄ መመለስ እንዳለበት ተገለጸ

የቡርጂ ዞን ሶያማ ዙሪያ ወረዳ ምክር ቤት 5ኛ ዙር 11ኛ የሥራ ዘመን 1ኛ መደበኛ ጉባኤ አካሂዷል፡፡

የወረዳው ዋና አፈ ጉባኤ አቶ እስራኤል ገብሬ በምክር ቤቱ የተነሱና በህብረተሰቡ ዘንድ ያሉ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን እና ሌሎች ጉዳዮችን ወስደን መሥራት አለብን ብለዋል፡፡

የቡርጂ ዞን ሶያማ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሰለሞን አኖ ለሁለት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የምክር ቤቱ ጉባኤ በዋናነት የህብረተሰቡ የመልካም አስተዳደርና የሰላም ጉዳዮች የተዳሰሱበት በመሆኑ ቀጣይ በህብረተሰቡ ውስጥ በመግባት ችግሮችን ለመፍታት መግባባት ላይ መደረሱን ገልፀዋል፡፡

የመልማት ጥያቄን ለመመለስ ወሳኙ ገቢ መሆኑን ጠቁመው አዳዲስ የተሾሙ አመራሮች ከህብረተሰቡ የሚነሱ ጉዳዮችን ለመፍታት በልዩ ትኩረት መሥራት ይጠበቅብናል ብለዋል።

በጉባኤው በ2016 በጀት ዓመት የነበሩ ጠንካራና ደካማ ጎኖች ተለይተው የተገመገሙ ሲሆን ለቀጣይ መሻሻል ያሉባቸውና መስተካከል የሚገባቸውን የሰላም፣ የመልካም አስተዳደር እና የልማት ጉዳዮች ተነስተው አቅጣጫ ተቀምጧል ብለዋል፡፡

በተለይም በደጋማው ቀበሌያት የመብራት፣ ንፁህ የመጠጥ ዉሃ፣ የኔትወርክ እና የመንገድ ልማት ችግር ዓመታትን ያስቆጠረ በመሆኑ ወረዳውና ዞኑ ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ ተጠይቋል፡፡

ከጉባኤው ተሳታፊ የምክር ቤት አባላት መካከል አቶ ታጋሽ ሶሮሞና አቶ በሪሶ ህርባዬ በምክር ቤቱና በሚመለከታቸው አካላት በተሠሩ ሥራዎች ለውጥ መታየቱን ጠቁመው ቀጣይ ሳይሳኩ በጅምር የቀሩ ተግባራት ትኩረት እንደሚሹ ተናግረዋል፡፡

ለህብረተሰቡ ሰላም ስጋት የሆነውን የውስጥና የውጪ ስጋት ለመቅረፍ እያንዳንዱ የምክር ቤት አባላትም ሆነ አመራሩ ከህብረተሰቡ ጋር ቀርበው መሥራትን ይጠይቃል ብለዋል፡፡

ለምክር ቤቱ መደበኛ ጉባኤ የሶያማ ዙሪያ ወረዳ የአስተዳደር፣ የምክር ቤቱና የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የ2016 ዓ.ም ሥራ አፈፃፀም ሪፖርት ቀርበው የተገመገሙ ሲሆን የተለያዩ ሹመቶችን በመስጠትና የ2017 በጀትን በማጽደቅ ጉባኤው ተጠናቋል፡፡

ዘጋቢ: ዮሴፍ ቶልኬ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን