የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የ2016 በጀት ዓመት አፈፃፀምና የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በሚዛን ከተማየውይይት መድረክ አካህዷል፡፡
መድረኩን የመሩት የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳጋቶ ኩምቤ እንደገለፁት ኢትዮጵያን ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ ጉልህ ሥራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ፡፡
በዚህም ከውጭ ሀገር የሚመጡ ባለሀብቶች ቁጥር እየጨመረ የመጣ ሲሆን በሀገር ውስጥ ያሉት ኢንቨስተሮች ላይም መነቃቃት ተፈጥሯል ብለዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም የውጪ ሀገራት አልሚ ባለሀብቶችን ለመሣብ በተደረገው ጥረት ከ10ሺህ በላይ ኢንቨስተሮች በ3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ዶላር ካፒታል የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንቶች ላይ ተሳትፈው ኢንቨስት እያደረጉ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡
በዘርፉ እየተከናወነ የሚገኘው አበረታች ሥራ በአፍሪካ ከግብፅና ከደቡብ አፍሪካ ቀጥሎ ሦሥተኛ ደረጃ ላይ በመሆን የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መዳረሻ ሀገር ተደርጋ እንድትቆጠር አድርጓታል ብለዋል አቶ ዳጋቶ።
ምክትል ኮሚሽነሩ አክለው በ2016 በጀት ዓመት 12 ሺህ አዳዲስ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገራት ባለሀብቶች ፍቃድ ማውጣታቸውን ጠቁመዋል።
በአዲሱ በጀት ዓመትም የውጭ ባለሀብቶችን በመሣብና የሀገር ውስጥ ባለሁበቶችን በማበረታታት የተጀመረውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፖሊሲ በመተግበር ሀገሪቱን ተጠቃሚ ለማድረግ በውይይቱ ከባለድርሻ አካላት ጋር መግባባት ላይ መድረሱንም አስረድተዋል።
ባለፉት ዓመታት በመስኩ ያጋጠሙትን እንደ መሰረት ልማትና መሬትን ከካሳ ነፃ አድርጎ ለኢንቨስተሮች ማሣለፍ ላይ የታዩት ተግዳሮቶችን በሚቀጥሉት ጊዜያት ለመፍታት አቅጣጫ መቀመጡንም ገልፀዋል ፡፡
በዘርፉ የታዩ ችግሮችን ለመፍታት የጋራ መግባባት ላይ መደረሱንም አብራርተዋል።
ዘጋቢ፡ ወሰኑ ወዳጆ- ከሚዛን

More Stories
የአፍላ ወጣቶችና ወጣቶችን የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ለመቅረፍ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጎልበት የጤና አደረጃጀቶችን ሚና ማሳደግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ
ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የመግባት ዕድል ያገኙ ተማሪዎች የበለጠ ውጤታማ ለመሆን ትምህርታቸው ላይ ብቻ ሊያተኩሩ እንደሚገባ መልዕክት ተላለፈ
የሀዲያ ዞን ፋይናንስ መምሪያ ለ2018 በጀት ዓመት ከ10 ቢልዮን ብር በላይ በጀት ለተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲውል በተገቢው እንደሚሠራ ገለፀ