የከተማውን ህዝብ ንፁህ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት ችግር ለመቅረፍ በትኩረት እየተሠራ መሆኑ ተገለፀ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 27/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የከተማውን ህዝብ የንፁህ መጠጥ ውሃ አገልግሎት ችግርን ለመቅረፍ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን በጌዴኦ ዞን የገደብ ከተማ አስተዳደር አስታውቋል።

በከተማው ከ1 መቶ 20 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ እየተሠራ ያለው የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት 91 በመቶ መጠናቀቁም ተገልጿል፡፡

የገደብ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ታሪኩ ሮቤ የከተማው ህዝብ ለበርካታ ዓመታት የንፁህ መጠጥ ውሃ አገልግሎት ጥያቄ ሲያነሳ መቆየቱን አንስተው ችግሩን ለመቅረፍ ከ1 መቶ 20 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እየተሠራ የሚገኘው የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት 91 ከመቶ ተጠናቆ በከፊል አገልግሎት መስጠት መጀመሩን አስታውቀዋል፡፡

የገደብ ከተማ አስተዳደር ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ደመቀ፤ ከአበዳሪ ተቋም እና በማችንግ ፈንድ በጀት እየተሠራ የሚገኘው ይህ ፕሮጀክት ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ ከ57 ሺህ በላይ የሚሆነውን የከተማውን የህብረተሰብ ክፍል የንፁህ መጠጥ ውሃ አገልግሎት ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

የፕሮጀክቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዮሴፍ ፍቃዱ በበኩላቸው ፕሮጀክቱ ወደመጠናቀቂያው ምዕራፍ መሸጋገሩን አንስተው የተሠሩ አዳዲስ የውሃ መተላለፊያ መሥመሮችን ከነባሮቹ ጋር በማገናኘት ህብረተሰቡ ሙሉ በሙሉ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆን ለማስቻል ቀሪ ሥራዎች በፍጥነት እየተከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ዘጋቢ: ሳሙኤል በቀለ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን