በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የጀመሩትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አሳሰበ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በሁለት ዞኖች ከ19 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ከ274 ሚሊዮን ብር በላይ የሚፈጅ የሃይላንድስ ሪዚሊያንስ አክቲቪቲ ፕሮጀክት በይፋ የማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሂዷል።

በመክፈቻ ፕሮግራሙ ላይ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ጋንታ ጋምአ እንደ ክልል በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ፕርጀክቱ አጋዥ በመሆኑ ለፕሮጀክቱ ሰኬታማነት ሁሉም ባለድርሻ አካላት መረባረብ አለባቸው ብለዋል።

በአሜሪካ መንግሥት ተራድኦ ድርጅት የሚደገፈው የሃይላንድ አክቲቪቲ ከገበያ ተዋናይ አካላት ጋር በመሥራት በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም የታቀፉ ቤተሰቦች የተሻለ ምርታማ እንዲሆኑ፣ አማራጭ የገቢ ምንጭ እንዲያገኙ፣ የንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ እንዲሳተፉና የሥራ ዕድል እንዲያገኙ እንደሚያግዝ የአሜሪካ መንግሥት ተራድኦ ድርጅት የኢትዮጵያ ተወካይ ዶ/ር ልዑልሰገድ በላይ ተናግረዋል።

የፕሮግራሙ ዋና ግብ በሀገር ደረጃ በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም የታቀፉ 120 ሺህ ቤተሰቦች በምግብ ራሳቸውን ችለው በዘላቂነት ከተረጂነት ተላቀው ከፕሮግራሙ መውጣት እንዲችሉ ማገዝ ነው ያሉት ደግሞ የሃይላንድ አክቲቪቲ ሪዚሊያንስ ፕሮጀክት ምክትል አስተባባሪ አቶ ጥላሁን አስማረ፤ ፕሮግራሙ በደቡብ ኢትዮጵያ 5 ወረዳዎች ተግባራዊ እንደሚሆን ገልፀዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል 19 ሺህ 487 ዜጎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግና ከ274 ሚሊዮን 529 ሺህ ብር በላይ እንደሚፈጅ የደቡብ ኢትዮጵያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ወ/ሮ ስምረት ሲማኖ ተናግረዋል።

በፕሮጀክቱ መክፈቻ ፕሮግራም ላይ የፓናል ውይይት የተደረገ ሲሆን የገበያ ተዋናይ አካላትም በምግብ ራስን ለመቻልና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገው እንቅስቃሴ ቀርቧል።

ዘጋቢ፡ አማሮ አርሳባ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን