የትምህርት ጥራትን ወደ ተሻለ ደረጀ ለማሳደግ የመረጃ ማዕከል ግንባታ ያለው ፋይደ ከፍተኛ መሆኑን የሆሳዕና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ገለጸ

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 25/2016 ዓ.ም (ደረቴድ) ኮሌጁ ከ40 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባውን የመረጃ ማዕከልና ለ27ኛ ጊዜ ያሰለጠናቸውን 561 ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡

የሆሳዕና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ምክትል ዲንና የመማር ማስተማር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ድንቁ ዳንኤል አለም አቀፋዊ የመረጃ ልውውጥ በማድረግ የትምህርት ጥራትን ወደ ተሻለ ደረጀ ለማሳደግ የመረጃ ማዕከሉ ግንባታ ያለው ፋይደ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።

ኮሌጁ በመማር ማስተማር፣ በምርምርና በማህበረሰብ አገልግሎት የሚያከናውናቸውን ተግባራት ለማሳለጥ ማዕከሉ አጋዥ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ኮሌጁ በዕለቱ በመጀመሪያ ድግሪ 141 ሰልጣኞችንና ለመጀማሪያ ጊዜ በድፕሎማ የትምህርት መርሀ ግብሮች 420 በድምሩ 561 ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡

በምረቃ ፕሮግራሙ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተደድር እና የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ እና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፍቃዱ፣ የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ሳሙኤል ዳርጌ እና ሌሎች የክልልና የዞን አመራሮች ተገኝተዋል፡፡

ዘጋቢ:-ሳሙኤል መንታሞ- ከሆሳዕና ጣቢያችን